• በቅርብ የተጻፉ

    Sunday 18 October 2015

    ንግሥት እሌኒና የመስቀሉ ታሪክ

    ዝንቱ መስቀል ቤዛነ ወመድሃኒትነ ለአይሁድ ስደተ ኮነ ወለነኒ ሕይወተ ኮነነ ዝንቱ መስቀል ተሰብሐ……………………/ቅዱስ ያሬድ/

    የመስቀሉ  በአይሁድ  መቀበር  መስቀል  የእግዚአብሔር  ታላቅ  ኃይሉ  የተገለጸበት  ዲያብሎስን  ያዋረደበት  ምእመናንን  የታደገበት  የሰላም  ዙፋን  ከመሆኑም  በላይ  በእለተ  አርብ  ቅዱስ  ሥጋው  የዋለበት፣  ካሣ  የተከፈለበት፣ወርቀ  ደሙ  የፈሰሰበት  ስለሆነ  እናከብረዋለን፡፡  እንሳለመዋለን፣  እንመካበታለን፡፡  የጸጋ  ስግደት እንሰግድለታለን፡፡ 

    ጌታችን  የተሰቀለበት  መስቀል  ሙት  እያስነሳ  ድውይ  እየፈወሰ  አጋንንት  እያወጣ  የተለያዩ  ገቢረ  ተአምራት  ሲሰራ  ሕዝቡ  አይተው  ክርስቲያን  እንዳይሆኑ  በመፍራት  በ 34 ዓ . ም  ከኢየሩሳሌም ወጣ  ብሎ  በሚገኝ  ቦታ  ቆፍረው  ቀበሩት፡፡  ከዚያም  የከተማውን  ቆሻሻ  ሁሉ  ከዚያ  መስቀሉ  በተቀበረበት  ቦታ  ላይ  እየደፉ  ከዘመን  ብዛት  ቦታው  በቆሻሻ  ክምር  የተነሣ  ተራራ  ሆነ፡፡  እስራኤልን  ከሮም  ቅኝ  አገዛዝ  ነጻ  ለማውጣት  ከ 66-70 ዓ . ም  ባደረጉት  እንቅስቃሴ  ጥጦስ  የተባለው  የሮም  ንጉሠ  ነገሥት  ዘምቶ  ኢየሩሳሌምን  በ 70 ዓ . ም  ደመሰሳት፡፡  ትልቁን  የአይሁድ  ቤተ መቅደስንም  አቃጠለው፡፡  እስራኤላውያንም  በመላው  ዓለም  ተበተኑ፡፡ 

    ከዘመነ  ሐዋርያት  ጀምሮ  በተከታታይ  በሮም  የነገሡ  ነገሥታት / ቄሳሮች /  በክርስቲያኖች  ላይ  የማያባራ  መከራ  አድርሰዋል፡፡  ክርስቲያኖች  የተቀበረውን  መስቀል  አስፈልገው  ለማውጣት  ቀርቶ  ሃይማኖታቸውን  የማመን  ነጻነት  ስላልነበራቸው  መስቀል  ለ 300  ዓመታት  ያህል  ተቀብሮ  የጉድፍ  መጣያ  ሆኖ  ቆየ፡፡  

    የመስቀሉ  የመገኘት  ታሪክ  የቤተክርስቲያን  የመከራ  ዘመን  አልፎ  የዕረፍትና  የሰላም  ዘመን  ሲመጣ  ለብዙ  ዘመን  ተቀብሮ  በሰው ዘንድ  እንደሞተ  ሰው  ከልብ  የተረሳውን  መስቀል  ባለቤቱ  መድኃኔዓለም  አልረሳምና  እሱ  የፈቀዳት  ዕለት  ስትደርስ  በዕሌኒ  ንግሥት  አማካኝነት  ከተቀበረበት  እንዲወጣ  አደረገ፡፡  ለዚህ  ታላቅ  ክብር  የተመረጠችው  ንግስት  ዕሌኒ  ለ 300  ዓመታት  የተቀበረውን  መስቀል  በኢየሱስ  ክርስቶስ  ፈቃድና  ኃይል  እንዴት  እንዳወጣች  ታሪኩን  ጠቅለል  አድርገን  እናቀርባለን፡፡ 

    ዕሌኒና  ተርቢኖስ  የሚባሉ  ሁለት  ደጋግ  ክርስቲያኖች  ተጋብተው  ይኖሩ  ነበር፡፡  ተርቢኖስና  ዕሌኒ  በኑሮአቸው  ፍቅርና  ሰላም  የሰፈነበት  በመሆኑ  ለብዙ  ሰዎች  እንደ  ምሳሌ  ሆነው  ይኖሩ  ነበር፡፡  ተርቢኖስ  ነጋዴ  ነበር፡፡  ራቅ  ወዳለ  ሀገር  በመርከብ  እየሄደ  በመነገድ  ይተዳደር  ነበር፡፡  ዕሌኒም  ባለቤቷ  ተርቢኖስ  ለንግድ  ወጥቶ  እስኪመለስ  ስለባሏ  ከመጸለይና  ከማሰብ  በቀር  ከግቢዋ  አትወጣም  ነበር፡፡ 

    አንድ  ጊዜ  ተርቢኖስ  ለንግድ  ሄዶ  ብዙ  ዓመታትን  ቆይቶከጓደኞቹ  ጋር  ወደ  ሀገሩ  ሲመለስከነጋዴዎች  አንዱ  በእግዚአብሔር ፈቃድ  ከሽፍታና  ከማዕበል  ከልዩ  ልዩ  አደጋ  ተርፈን  በሰላም  ተመልሰን  ግን  ሚስቶቻችን  ሌላ  ሳይወዱ  ሳይለምዱ  እናገኛቸው  ይሆን ?  ብሎ  ጠየቀ፡፡  ተርቢኖስ  ግን " እንኳን  በሰላም  አደረሰን  እንጂ  ሚስቴን  በዚህ  አልጠረጥራትም "  ብሎ  ሲመልስ  ሌላው  ጓደኛው " ያንተ ሚስት  ከማንትበልጣለችና  ነው  አሁን  ሄጄ  ከሚስትህ  ጋር  ለምዳኝ  ወዳኝ  ወድጃት  ብመጣስ  ምን  ይቅጣህ ?"  አለው፡፡  ተርቢኖስም  በሚስቱ  እሌኒ  ተማምኖና  ይህንን  ብታደርግ  ይህን  ያህል  ዓመት  የለፋሁበት  ሀብት  ከነትርፉ  ውሰድ  አንተም  ብታደርግ  እንዲሁ  ሀብትህ  ከነትርፉ  ለእኔ  ይሁን  ተባብለው  ተወራረዱ፡፡  ከዚያም  መርከቡ  ወደብ  ከመድረሱ  በፊት  ነጋዴው  ወደ  ዕሌኒ  ቤት  ደረሰና  በሩን  አንኳኩቶ  ሠራተኛይቱን  ዕሌኒን  ማነጋገር  እፈልጋለሁና  ንገሪልኝ  ብሎ  ጠየቃት፡፡  እሷም  እያፈረች  የተላከችውን  ለዕሌኒ  ነገረቻት  ዕሌኒም  ተቆጥታ  ከመች  ወዲህ  ነው እንግዳ  የማነጋግረው  ብላ  አሳፈረታቸው፡፡  ሠራተኛይቱም  ለነጋዴው  መልሱን  ስትነግረው  ነጋዴው  እንደማይሆንለት  ከተረዳበኋላ  ሌላ  ተንኮል  አቀደና  ለሠራተኛይቱ  ባልና  ሚስቱ  ብቻ  የሚያውቁትን  አንድ  ነገር  ብቻ  ብትሰጪኝ  ብዙ  ገንዘብ  ወርቅ  እሰጥሻለሁ  ብሎ  ወርቅ  ሰጣት፡፡  ሠራተኛይቱም  ሁለቱ  ብቻ  የሚያውቁትን  የእመቤቴ  ሀብል  አለ  ያንን  እመጣልሀለሁ  መጀመርያ  አንተ  በከተማው  ውስጥ  እየዞርህ  ነጋዴዎችን  መጡ  የብስ  ረገጡ  እያልክ  አስወራ  ከዚያም  ተመልሰህ  እንድትመጣ  ብላ  ሰደደችው፡፡ 

    ነጋዴውም  እንደተመከረው  የነጋዴዎቹን  መምጣት  በከተማይቱ  እንዳወራ  የነጋዴዎቹ  ቤተሰቦች  ነጋዴዎችን ለመቀበል  ዝግጅት  ማድረግ  ጀመሩ፡፡  የዕሌኒም  ሰራተኛ  እመቤቴ  ነጋዴዎች  መጡ  ተብሎ  ይወራልና፡፡  ባለቤትዎ  በሰላም  ስለመጡ  ይዘገጃጁ  ገላዎን  ይታጠቡ  ብላ  መከረቻት፡፡  ዕሌኒም  ገላዋን  ስትታጠብ  ያንገቷን  ሐብል  ቁጭ  ካደረገችበት  ቦታ  ሠራተኛይቱ  አንስታ  ለነጋዴው  በተቃጠሩበት  ዕለት  ሰጣች፡፡  ነጋዴውም  ለሠራተኛይቱ  የውለታዋን  ብዙ  ገንዘብ  ሰጥቶአት  ደስ  እያለው  ወደ  ጓደኞቹ  ሄደ፡፡  ለተርቢኖስ  ሚስትህን  ለምጃት  ወድጃት  መጣሁ  አለው  ተርቢኖስም  ውሸት  ነው  ለዚህ  ምን  ምልክት  አለህ  ብሎ  ጠየቀው፡፡  ተንኮለኛውም  ነጋዴ  ያንን  ሐብል  አውጥቶ  ይህ  ሐብል  የሚስትህ  አይደለምን  ብሎ  ሰጠው  ተርቢኖስም  ደነገጠ  የሚናገረው  አጣ፡፡  በውርርዱም  ሀብቱን  ሁሉ  አስረከበና  ባዶ  እጁን  ወደቤቱ  እያዘነ  እየተቆጨ  ሔደ፡፡  ባለቤቷን  በናፍቆትና  በታማኝነትስትጠብቅ  የከረመችው  ዕሌኒ  በተርቢኖስ  ያልተለመደ  ሀዘንና  ብስጭት  ግራ  ተጋብታ  ወንድሜ  ምንሆነሀል ?  ለወትሮው  እንኳን  ይህንያህል  ዘመን  ተለያይተን  ቀርቶ  ለጥቂት  ቀናት  ተለያይተን  እንኳ  ለጥቂት  ቀናት  ተለያይተን  ስንገናኝ  እንነፋፈቃለን፡፡  አሁን  ግን  ከመጣህበት  ጊዜ  ጀምሮአዝነህ  አይሀለሁ  ብላ  ጠየቀችው፡፡ 

    ተርቢኖስም  ብዙ  የደከምኩበትና  የለፋሁበት  ሀብትንብረቴ  እንዳለ  ማዕበል  አጠፋብኝ  እኔ  ያላዘንኩ  ማን  ይዘን  አላት፡፡  እሌኒም  የተማረች  ናትና  እግዚአብሔር  ሰጠ  እግዚአብሔር  ነሣ  የእግዚአብሔር  ስም  የተመሰገነ  ይሁን  እንዳለ  ኢዮብን  አስበው  አንተ  እንኳን  በሰላም  መጣህ  እንጂ  ሀብቱ  ውሎ  አድሮ  ይመጣል፡፡  እያለች  አጽናናችው፡፡  ተርቢኖስም  እንግዲህ  በተከበርኩበት  ሀገር  ተዋርጄ፣  በሰጠሁበት  ሀገር  ለምኜ  ለመኖር  አልችልምና  ወደሌላ  ወደማያውቁኝ  ሀገር  እሔዳለሁ  አንቺ  ግን  ሁሉ  ይወድሻል  ያከብርሻል  ከወደድሸውጋር  ኑሪ  አላት፡፡  ዕሌኒም  በደስታ  ጊዜ  አብሬህ  እንደሆንኩ  በችግርም  ጊዜ  ልለይህም  የኔንና  ያንተን  አንድነት  ችግር  አይፈታውም  ከአንተ  ተለይቼ  ወዴት  እቀራለሁ  ወደ ምትሄድበት  አብሬህ  እሄዳለሁ  ብላ  ተነሳች፡፡ 

    ሁለቱም  ቤታቸውን  ጥለው  ሲሄዱ  በመንገድ  ላይ  ተርቢኖስ  በልቡናው  ይዞት  የነበረውን  ምሥጢር  አወጣው " ዕሌኒ  ስወድሽ  የጠላሽኝ  ሳምንሽ  የከዳሽኝ  ምን  አድርጌሽ  ነው ?"  ብሎ  ጠየቃት፡፡  ዕሌኒም  እኔ  አንተን  አልጠላሁም  አልከዳሁምም  ይህንን  ሐሳብ  እንዴት  አሰብህ  ብትለው  ከኪሱ  አውጥቶ  ሐብሉ  አሳያትና  የሆነውን  ሁሉ  ነገራት፡፡  ዕሌኒም  ያልጠበቀችውን  ነገር  ስለተፈጸመ  አዝና  የሆነውን  እውነተኛ  ታሪክ  በሙሉ  ነገረችው፡፡  ተርቢኖስ  ግን  አላመናትም፡፡  ከባህር  ዳር  በደረሱ  ጊዜ  በቁመቷ  ልክ  ሳጥን  አሠርቶ  ዕሌኒን  በውስጡ  አስገባትና  ብታደርጊውም  ባታደርጊውም  እንደሥራሽ  ሥራሽ  ያውጣሽ  ብሎ  ወደ  ባህሩ  ወረወራት፡፡  ዕሌኒ  ያለችበት  ሳጥን  በፈቃደ  እግዚአብሔር  እየተንሳፈፈ  ከወደብ  ደረሰ  በዚያ  ወደብ  አካባቢ  ምዕራብ  ሮምን  ያስተዳደር  የነበረው  ኮስታንዲዮስ / ቁንስጣ /  የተባለው  ንጉሥ  ነበርና  ሳጥኑን  አይቶ  አውጥቶ  እንዲከፍቱት  ወታደሮችን  አዘዘ፡፡  ሳጥኑን  አውጥተውም  ሲከፍቱት  እጅግ  የተዋበች  ሴት  ሆና  አገኟት  ንጉሡም  ዕሌኒን  ወስዶ  ሚስቱ  አደረጋት፡፡ 

    ኮስታንዲዮስ / ቁንስጣ /  የመክስምያኖስ  ቄሳር  ሆኖ  ምዕራብ  ሮምን  ያስተዳደር  ነበር፡፡  ንግስት  ዕሌኒም  በ 272 ዓ . ም  ታላቁ  ቆስጠንጢኖስን ወለደችለት  ቆስጠንጢኖስም  ገና  በወጣትነቱ  የአባቱ  እንደራሴ  ሆኖ  እንዳሠራ  አባቱ  ሞተ፡፡  የአባቱ  ባለሟሎችና  ህዝቡ  ተስማምተው  የ 18  ዓመቱን  ቆስጠንጢኖስን  በአባቱ  ቦታ  ሐምሌ 25  ቀን 300 ዓ . ም  በሮም  ምዕራብ  ክፍል  በገላትያ  አነገሡት፡፡  በጦር  ሜዳዎች  ብዙ  የጀግንነት  ሥራዎች  ስለሰራ  በሠራዊቱ  ዘንድ  ይወደድ  ነበር፡፡  ንግሥት  ዕሌኒ  ልጅዋን  ቆስጠንጢኖስን  ከልጅነቱ  ጀምሮ  ስለክርስትና  ሃይማኖትና  ስለክርስቲያኖች  መከራ  ታስተምረው  ስለነበር  በክርስቲያኖች  ላይ  የነበረው  አመለካከት  በሮም  ከነገሡት  ቄሣሮች  ሁሉ  የተሻለ  ነበር፡፡  በተለይም  በ 312 ዓ . ም  ከጠላቱ  ከመክስምያኖስ  ጋር  ለመዋጋት  ምታ  ነጋሪት  ክተት  ሠራዊት  ብሎ  ለዘመቻ  እንደተሰለፈ  በራዕይ  በሰማይ  ላይ " በዚህ  መስቀል / ምልክት /  ጠላትህን  ድል  ታደርጋለህ "  የሚል  መስቀልና  ጽሑፍ  ስላየ  ለሠራዊቱ  የመስቀል  ምልክት  በመሳሪያቸው  እና  በሰንደቅ  ዓላማው  ላይ  እንዲያደርጉ  አዘዘ፡፡  ወደያው  ጦርነት  ቢገጥም  በቲቤር  ወንዝ  ድልድይ  ላይ  ጠላቱን  ድል  ነስቶ  በጠቅላላው  የሮም  መንግስት  ግዛቶች  ሁሉ  ገዥ  ሆነ፡፡ 

    ታላቁ  ቆስጠንጢኖስ  የሮም  ንጉሠ  ነገሥት  ከሆነ  በኋላ  በ 300  ዓመታት  ውስጥ  ለመጀመርያ  ጊዜ  ለክርስቲያኖች  የነጻነት  ዐዋጅ  ዐወጀ፡፡  ክርስትናም  ብሔራዊ  ሃይማኖት  ተባለች፡፡  ንግሥት  እሌኒም  በተፈጠረላት  አመች  ሁኔታ  በመጠቀም  የጌታችን  መስቀል  ከተቀበረበት  ለማውጣት  በ 327 ዓ . ም  ወደ  ኢየሩሳሌም  ሔደች፡፡  ዕሌኒ  ልጅዋ  ቆስጠንጢኖስ  ክርስቲያን  ከሆነላት  ወደ  ኢየሩሳሌም  ሔዳ  መስቀሉን  ለመፈለግ  እንዲሁም  በኢየሩሳሌምያሉ  ቅዱሳት  መካናትንና  አብያተ  ክርስቲያናትን  ከማነጽ  ለእግዚአብሔር  ተሳለች፡፡  ከዚህ በኋላ  ቆስጠንጢኖስ  አምኖ  በ 337 ዓ . ም  ተጠመቀ፡፡ 

    ቅድስት  ዕሌኒ  ወደ  ኢየሩሳሌም  ሔደች  ከእርሷም  ጋር  ብዙ  ሠራዊት  ነበር፡፡  እንደደረሰችም  ስለ  ከብረ  መስቀል  መረመረች  ጠየቀች፡፡  ቦታውን  የሚያስረዳት አላገኘችም፡፡  የአይሁድ  ወገን  እንቢ  ቢሉም  በኋላ  ግን  ባደረገችው  ጥረት  አረጋዊው  ኪራኮስ  የጎልጎታን  ኮረብታ  አመለከታት  አስቆፍሪው  ብሎ  ነገራት  ኪራኮስም  ዘመኑ  ከመርዘሙ  ጋር  ተያይዞ  እውነተኛው  ተራራ  ይህ  ነው  ብሎ  ማሳየት  ባለመቻሉ  ከሦስቱ  ተራሮች  አንዱ  ነው  ስላላት  አይሁድ  ተራሮቹን  ይቆፍሩ  ዘንድ  አዘዘቻቸው፡፡ 

    የጌታችን  ቅዱስ  መስቀል  ከጌታ  ሞት  እያመነ  በተቸገሩ  ግዜ  ማንም  እንዳያገኘው  የኢየሩሳሌም  ነዋሪሁሉ  የእቤቱን  ቆሻሻ  የከበረ  መስቀል  ባለበት  ቦታ  እንዲጥል  አይሁድ  አዝዘው  ስለነበር  ከሁለት  መቶ  ዓመት  በላይ  ጥራጊ  ስለጣሉበት  ታላቅ  ተራራ  ሆነ፡፡  ዕሌኒ  ተራሮቹን  ለማስቆፈር  ከሦስቱ  ተራሮች  የቱ  እንደሆነ  ለመለየት  ደመራ  አስደምራ  ብዙ  እጣንም  በመጨመርና  በማቃጠል  ምልክት  አገኘች፡፡  እርሱም  የእጣኑ  ጢስ  ወደ  ሰማይ  በመውጣትበቀጥታ  ተመልሶ  መስቀሉ  ባለበት  ተራራ  ላይ  በማረፍና  በመስገድ  መስቀሉ  ያለበትን  ትክክለኛ  ስፍራ  አመለከታት፡፡  ቅዱስ  ያሬድም " ሰገደ  ጢስ "  ጢሱ  ሰገደ  ብሎታል፡፡  ከዚያም  መስከረም 16 ቀን  ቁፋሮው  እንዲጀመር  አዘዘች፡፡  ሰባት  ወር  ያህል  ከተቆፈረ  በኋላ  መጋቢት 10  ቀን  ሦስት  መስቀሎች  በአንድነት  ተገኙ፡፡ 

    የክብር  ባለቤት  ጌታችን  የተሰቀለበት  የትኛው  እንደሆነ  ለማወቅ  ተቸገሩ፡፡  አንድ  የሞተ  ሰው  አምጥተው  በሁለቱ  መስቀሎች  ላይ  በተራ  ቢያስቀምጡት  አልተነሣም፡፡  ለመጨረሻ  ግዜ  በአንዱ  መስቀል  ላይ  ቢያስቀምጡት  ያን  ጊዜ  የሞተው  ሰው  ተነሣ፡፡  በዚህም  የጌታን  መስቀል  ለይታው  አገኘች፡፡  ዕሌኒም  የጌታ  መስቀል  እንደሆነ  አወቀ  ሰገደችለት፡፡  ክርስቲያኖች  ሁሉሰገዱለት፡፡  በየሀገሩ  ያሉ  ክርስትያኖች  ሁሉ  የመስቀሉን  መገኘት  በሰሙ  ግዜ  መብራት  አብርተው  ደስታቸውን  በመግለጥ  ለዓለም  እንዲታወቅ  አደረጉ፡፡  በዚህም  ምክንያት  ይህንን  ታላቅ  የድኅነት  ምልክት  የሆነው  መስቀል  የኢትዮጵያ  ቤተክርስትያን  ደመራ  በመደመር  በታላቅ  መንፈሳዊ  ሥነ  ሥርዓት  ታከብረዋለች፡፡ 

    ዳግማዊ  ጐልጐታ  ግሸን  ደብረ  ከርቤ  በወሎ  ክፍለ  ሀገር  በአንባሰል  አውራጃ  ውስጥ  ግሸን  ማርያም  የምትባል  ደብር  ትገኛለች፡፡  ይህች  ደብር  በሐይቅና  በመቅደላ  በደላንታ  በየጁ  መካከልና  በበሽሎ  ወንዝ  አዋሳኝ  በርዋ  አንድ  ዙርያውን  በገድል  የተከበበች  አምባ  ናት፡፡  በበርዋ  ከተገባ  በኋላ  ግቢዋ፣  ከላይ  ሜዳና  መስቀለኛ  ቦታ  ነው፡፡  ወደዚህች  ደብር  ለመሔድ  በረሃን  አቋርጦ  ተለያየን  ወንዝና  በሽሎን  በመሻገር  የተጠማዘዘ  አስፈሪ  ገደሉን  ማለፍ  ግድ  ይላል፡፡  ግሸን  የመጀመርያ  ስሟ  ደብረ  እግዚአብሔር  በመባል  ይጠራ  ነበር፡፡  ይህ  ደብረ  እግዚአብሔር  የሚለው  ስያሜም  በጻድቁ  ንጉሥ  ላሊበላ  እጅ  ከቃጥኝ  ድንጋይ  ተፈልፍሎ  የተሠራ  ቤተመቅደስ  በእግዚአብሔር  አብ  ስም  ስለነበረ  ደብረ  እግዚአብሔር  ተብሎ  የተጠራ  ነበር፡፡  ከዚያም  በዓጼ  ድግናዥን  ዘመነ  መንግሥት  የሐይቅ  እስጢፋኖስ  ገዳም  ሲመሰረት  ሐይቅ  ደብረ  ነጐድጓድ  ተብሎ  ሲሰየም  ግሸን  የሐይቅ  ግዛት  ስለሆነች  ደብረ  እግዚአብሔር  ተብላለች፡፡  ከዚያም  በ 14 ኛው  መቶ  ከፍለ  ዘመን  ላይ  በዓጼ  ዘርአያዕቆብ  ዘመነ  መንግስት  የክርስቲያን  ግማደ  መስቀሉ  ግሸን  ገብቶ  ሲቀመጥ  ከደብረ  ነጐድጓድ  ደብረ  ከርቤ  ተብላለች፡፡  የደብሩ  አስተዳዳሪም  መምህረ  እስራኤል  ዘደብረ  ከርቤ  ይባል  ነበር፡፡  ከደብረ  ከርቤ  ግሸን  ማርያም  ተብላለች፡፡ 
    መስቀሉ  ወደ  ግሸን  አምባ  የመውጣቱ  ታሪክ 

    ንግሥት  ዕሌኒ  መስከረም 16  ቀን 320 ዓ . ም  በዕጣን  ጢስ  ምልክት  ቁፋሮ  አስጀምራ  መጋቢት 10  ቀን  አግኝታ  በማውጣት  ታላቅ  ቤተመቅደስ  ጎልጎታ  ላይ  ሠርታ  በክብር  አስቀመጠችው  ይህ  መስቀልም  ከዚያ  ዕለት  ጀምሮ  እንደ  ፀሐይ  እያበራ  ድውይ  እየፈወሰ  አጋንንት  እያባረረ  ልዩ  ልዩ  ተአምራት  እየሰራ  ሙት  እያነሳ  ዕውር  እያበራ  ተአምራቱን  ቀጠለ፡፡  ይህንንም  ከኃያላን  ነገሥታት  መካከል  የፋርስ  ንጉሥ  መስቀሉን  ማርኮ  ፋርስ  ወስዶ  አስቀመጠው፡፡  በዚህ  ጊዜ  የአየሩሳሌም  ምዕመናን  የድሉን  ዜና  ሰምተው  ስለነበር  የአንድ  ቀን  መንገድ  ያህል  ሄደው  በመቀበል  ካህናቱ  በዝማሬና  በቸብቸቦ  ወንዱ  በሆታ  ሴቱ  በእልልታ  ሆ !  እያሉና  ችቦ  አብርተው  ተቀብለዋቸዋል፡፡  የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ  ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያኖችም  ለመስቀል  ችቦእያበሩ  በዓሉን  በሆታ  በእልልታ  በስብሐተ  እግዚአብሔር  የሚያከብሩት  ይህንን  ታሪካዊ  ትውፊት  በመከተል  ነው፡፡ 

    ብዙ  የቤተክርስቲያን  አባቶች  እንደሚሉት  ንጉሡ  ሕርቃል  ይህንን  ታላቅ  ድል  ለማግኘትና  የጌታን  ቅዱስ  መስቀል  ከአሕዛብ / ከፋርሶች /  እጅ  ለማስመለስ  የቻለው  በዚያን  ጊዜ  አብያተ  ክርስቲያንናት  ሁሉ  ለአንድ  ሳምንት / አንድ  ሱባዔ /  ባደረጉትጾም  ጸሎት  ነው፡፡  ይህንንም  ለማስታወስና  ጌታን  ለማመስገን  የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ  ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያንና  የግብጽ  ኮፕቲክቤተክርስቲያን  በየዓመቱ  የዐቢይጾም / የጌታ  ጾም /  ከመጀመሩ  አስቀድሞ " ጾመ  ሕርቃል "  ብለው  አንድ  ሳምንት  ይጾማሉ፡፡ ፓትርያርክ  ተረክቦ  ወስዶ  በክብር  አስቀመጠው፡፡ 

    ይህ  ግማደ  መስቀልም  ለብዙ  ዘመን በእስክንድርያ  ሲኖሩ  በግብጽ  ያሉ  እስላሞች  እየበዙ  ኃይላቸው  እየጠነከረ  ሔደ  በእስክንድርያ  የሚኖሩትን  ክርስትያኖች  ላይ  ሥቃይ  ያጸኑባቸው  ጀመር፡፡  ክርስቲያኖቹም  አንድ  ሆነው  መክረው  ለኢትዮጵያዊው  ዓጼ  ዳዊት  እንዲህ  የሚል  መልእክት  ላኩ " ንጉሥ  ሆይ !  በዚህ  በግብጽ  ያሉ  እስላሞች  መከራ  አጽንተውብናል  ኃይልህን  አንሥተህ  አስታግስልን  ብለው  ጠየቁት  ዳግማዊ  ዓጼ  ዳዊትም  ለመንፈሳዊ  ኃይማኖት  ቀንተው  የክርስቶስ  ፍቅር  አስገድዷቸው 20,000  ሠራዊት  አስከትለው  ወደግብጽ  ዘመቱ  በዚህ  ጊዜ  በግብጽ  ያሉ  ኃያላን  ፈሩ  ተሸበሩ  ንጉሡ  ዳግማዊ  ዳዊትም  እንዲህ  የሚል  መልዕክት  ለእስላሞቹ  ላከ  በተፈጥሮ  ወንድሞቻችሁ  ከሆኑት  ክርስቲያኖች  ካልታረቃችሁ  ሀገራችሁን  መጥቼ  አጠፋለሁ "  የሚል  ማስጠንቀቂያ  ላከ፡፡ 

    የንጉሡ  መልዕክትም  ለእስላሞቹ  እንደደረሳቸው  ፈርተው  እንደ  ጥንቱ  በየሃይማታቸው  ጸንተው  በሰላም  እንዲኖሩ  ከክርስቲያን  ወንድሞቻቸው  ጋር  ታረቁ፡፡  መታረቃቸውን  ዓጼ  ዳዊት  ሰሙ  በዚህም  ጉዳይ  ንጉሡ  ደስ  አላቸው፡፡  እግዚአብሔር  አመሰገኑ  በግብጽ  የሚኖሩ  ክርስቲያኖችም  ከ 12,000  ወቄት  ወርቅ  ጋር  ደስታቸውን  ለኢትዮጵያዊው  ንጉሥ  ለዳግማዊ  ዳዊት  በደብዳቤ  አድርገው  ላኩላቸው፡፡  ንጉሡም  የደስታውንደብዳቤ  ተመልክተው  ደስ  አላቸው  ወርቁን  ግን  መልሰው  በመላክ  እንዲህ  የሚል  ደብዳቤ  ጻፉ፡፡  በግብጽ  የምትኖሩ  የክርስቶስ  ተከታዮች  ሆኖ  እንኳን  ደስ  አላችሁ  የላካችሁልኝ 12,000  ወቄት  ወርቅ  መልሼ  ልኬላችኋለሁ፡፡  የእኔ  ዓላማ  ወርቅ  ፍለጋ  አይደለም  የክርስቶስ  ፍቅር  አስገድዶኝ  በተቻለኝ  ችግራችሁን  ሁሉ  አስወገድኩላችሁ  አሁንም  የምለምናችሁ  በሀገሬ  ኢትዮጵያ  ረሀብና  ቸነፈር  ድርቅ  ስለወረደብኝ  መድኃኒታችን  ኢየሱስ  ክርስቶስ  የተሰቀለበት  ቅዱስ  መስቀልና  የቅዱሳን  አጽም  ከሌሎች  ክቡራን  ዕቃዎች  ጋር  እንድትልኩልኝ  ነው  የሚል  ነበር፡፡  በእስክንድርያም  ያሉ  ምዕመናን  ይህ  መልዕክት  እንደደረሳቸው  ከሊቃነ  ጳጳሳትና  ከኤጲስ  ቆጶሳቱ  ጋር  ውይይት  በማድረግ  ይህ  ንጉሥ  ታላቅ  ክርስቲያን  ነው፡፡  ስለዚህ  ልቡን  ደስ  እንዲለው  የፈለገውን  የጌታችንን ግማደ  መስቀል  ከቅዱሳን  አጽምና  ንዋየ  ቅዱሳት  ጋር  አሁን  በመለሰው  ወቄት  ወርቅ  የብርና  የነሐስ  የመዳብና  የወርቅ  ሣጥን  አዘጋጅተን  እንላክለት  ብለው  ተስማምተው  በክብር  በሥነ  ሥርዓት  በሠረገላና  በግመል  አስጭነው  ስናር  ድረስ  አምጥተው  ባስረከቧቸው  ጊዜ  በእጃቸው  እያጨበጨቡ  በእግራቸው  እያሸበሸቡ  በግንባራቸው  እየሰገዱ  በክብር  በደስታ ተቀበሏቸው፡፡  መስከረም 16  በኢትዮጵያ  ታላቅ  ብርሃን  ሌሊትና  ቀን  ሦስት  ቀን  ሙሉ  ሲበራ  ሰነበተ፡፡ 

    ግማደ  መስቀሉ  ወደ  መካከለኛው  ኢትዮጵያ  ሳይደርስ  በድንገት  ዓጼ  ዳዊት  ስናር  ላይ  አረፉ፡፡  ግማደ  መስቀሉም  የግድ  በዚያው  በስናር  መቆየት  አስፈለገው፡፡  ከዚህ  በኋላ  የሟቹ  የዳግማዊ  ዳዊት  ልጅ  ዓጼ  ዘርዓ  ያዕቆብ  እንደነገሠ  ወደ  ስናር  ሔደ  ግማደ መስቀሉን  ከሌሎቹ  ንዋያተ  ቅዱሳት  ጋር  አምጥተው  በመናገሻ  ከተማቸው  በደብረ  ብርሃን  ላይ  ቤተመቅደስ  ሠርተው  ለማስቀመጥ  ሲደክሙ  በሕልማቸው  አንብር  መስቀልየ  በዲበ  መስቀል  ወዳጄ  ዘርዐ  ያዕቆብ  ሆይ  መስቀሌን  በመስቀለኛ  ቦታ  ላይ  አስቀምጥ  የሚል  ሕልም  አየ፡፡  ንጉሡም  መስቀለኛ  ቦታ  እየፈለጉ  በኢትዮጵያ  አውራጃዎች  ሁሉ  በመፈለግ  ከብዙ  ቦታ  አስቀምጠውት  ነበር፡፡  ለምሳሌ  በሸዋ  በደርሄ  ማርያም፣  በማናገሻ  ማርያም፣  በወጨጫ  መስቀሉን  አሳርፈውት  ነበር፡፡  ነገር  ግን  የመጨረሻውን  ቦታ  ባለማግኘታቸው  በራዕይ  እየደጋገመ  መስቀሌን  በመስቀለኛ ሥፍራ  አስቀምጥ  እያለ  ይነግራቸው  ነበር፡፡  ዓጼ  ዘርዓ  ያዕቆብም  ለሰባት  ቀን  ሱባዔ  ገቡ፡፡  በዚያም  የተገለጸላቸው  መስቀለኛውን  ቦታ  የሚመራህ  ዓምደብርሃን  ይመጣል  አላቸው፡፡ እርሳቸውም  ከዚያ  እንደወጡ  መስቀለኛውን  ቦታ  የሚመራ  የብርሃን  ዓምድ  ከፊታቸው  መጥቶ  ቆመ፡፡  በዚያ  መሪነት  ወደ  ወሎ  ክፍለ  ሀገር  አምባሰል  አውራጃ  ውስጥ  ግሸን  ከምትባል  አምባ  መርቶ  አደረሳቸው፡፡  በእውነትምይህች  ግሸን  የተባለችው  አምባ  ጥበበኛ  ሰው  እንደቀረጻት  የተዋበች  መስቀለኛ  ቦታ  ሆና  ስላገኟት  የልባቸው  ስለደረሰ  ደስ  አላቸው፡፡  በዚያም  አምባ  ታላቅ  ቤተመቅደስ  ሰርተው  መስቀሉንና  ሌሎች  ንዋየ  ቅዱሳቱን  በየመዓረጋቸው  የክብርቦታ  መድበው  አስቀመጡዋቸው፡፡ 

    ዘመኑም  በ 14 ኛው  ክፍለ  ዘመን  ነው፡፡  ከእስክንድርያ  ሀገር  ከመስቀሉ  ጋር  በልዩ  ልዩ  ሣጥን  ተቆልፈው  የመጡትም  ዝርዝር  ስማቸው  ጌታ  በዕለተ  ዓርብ  ለብሶት  የነበረው  ቀይ  ልብስ፣  ከሮም  የመጣው  ከለሜዳው፣  ሐሙት  የጠጣበት  ሰፍነግ / ጽዋ / ፣  ዮሐንስ  የሳለውኩርዓተ  ርዕሱ  ስዕል  እንዲሁም  የተለያዩ  የቅዱሳን  አጽም፣  ከግብጽ  ታላላቅ  ገዳማት  የተቆነጠረ  አፈር፣  የዮርዳኖስ  ውሃ  ይገኛል፡፡ 

    መስቀሉ  በእኛ  ሕይወት

    በመስቀሉ  ድነናል  ኤፌሶን 1 ፡ 7 ፤ 1 ኛ .  ጴጥ . 1 ፡ 19 
    በመስቀሉ  ክርስቶስ  ወደ  ራሱ  አቅርቦናል፤  በሰማያት  ወደ  አባቱ  አቅርቦናል  ዮሐ . 12 ፡ 32  ፣ኤፌሶን 2 ፡ 13 ፣  መጽ . ኪዳን 
    በመስቀሉ  ከእግዚአብሔር  ጋር  ታርቀናል  ሰላምን  አግኝተናል  ሮሜ . 5 ፡ 2 ፣ 1 ቆሮ . 1 ፡ 31 ፣  ዕብ .10 ፡ 10 
    በመስቀሉ  ለዘለዓለም  ፍጹማን  ሆነናል  ዕብ .10 ፡ 14 
    በመስቀሉ  የዕዳ  ደብዳቤያችን  ተደምስሰዋል  ቈላ . 2 ፡ 14 
    በመስቀሉ  ወደ  ቅድስተ  ቅዱሳንለመግባት  ሞገስ  አግኝተናል፣  ዕብ .10 ፡ 19 
    በመስቀሉ  ላይ  በፈሰሰው  ደም  ከበደላችን  ሁሉ  ታጥበናል  ራዕ . 12 ፡ 11 
    በመስቀሉ  ቤዛነት  እንመካለን  ገላ . 6 ፡ 14 

    ዛሬ  ያለው  የመስቀል  አከባበር  በግሸን 

    ከላይ  ለመጥቀስ  እንደሞከርኩት  ግሸን  አምባ  ከአዲስ  አበባ 480  ኪሎ  ሜትር  ርቀት  ላይ  የምትገኝ  ቅድስት  ሥፍራ  ናት፡፡  ጥንት  በአባቶቻችን  ዘመን  ለጊሸን  ማርያም  ክብረ  በዓል  ጉዞ  የሚጀመረው  ከአንድ  ወር  በፊት  ሲሆን  መንገዱም  አመቺ  ባለመሆኑ  አስቸጋሪ  ነበር፡፡  በተለይም  በአሁን  ወቅት  ከሀገር  ውስጥም  ይሁን  ከሀገር  ውጭ  ያሉ  ክርስቲያኖች  ለመሳለምና  ለመባረክ  ዕቅድ  ይዘው  መምጣት  ጀምረዋል፡፡  ቁጥራቸው  ጥቂት  የማይባሉ  በብዙ  መቶ  ሺህ  የሚቆጠሩ  ምዕመናን  ወደ  ሥፍራው  ይጓዛሉ፡፡  ጉዞውም  በትራንስፖርት  የታገዘ  በመሆኑናእስከ  ተራራው  ጥግ  መኪና  ስለሚደርስ  ጉዞው  ብዙም  አያስቸግርም፡፡  ብዙ  ምዕመናንምእየዘመሩ፣  እየተማማሩ  በማኅበር መጓዝ  የተለመደ  ነው፡፡  መግቢያ  በሩ  ጠባብና  አንድ  ብቻ  በመሆኑ  ለመተላለፍ  ቢያስቸግርም  በተለያዩ  ማኅበራት  የሚጓዙ  ወጣቶች  ደከመኝ  ሰለቸኝ  ሳይሉ  የሚወጣና  የሚወርደውን  ምዕመን  ሌትና  ቀን  በማስተባበር  ይሰራሉ፡፡  በጊሸን  አምባ  በሁሉም  ማዕዘን  አብያተ  ክርስቲያናት  የታነፁ  ሲሆን  ከመስቀሉ  ራስጌ  የእመቤታችን፣  ከመስቀሉ  ግርጌ  የቅዱስ  ሚካኤል  ከቀኝ  ክንፉ  ላይ  ቅዱስ  ገብርኤልከግራ  ክንፉ  ደግሞ  ቅዱስ  ዑራኤል ሲሆኑ  መካከሉ  ላይ  መስቀሉ  የተቀበረበት  የእግዚአብሔር  አብ ቤተክርስቲያን  ይገኛል፡፡  በተለይም  መስከረም 21  ቅዳሴ  ለማስቀደስ  ቅዱስ  ቁርባን  ለመቀበል  የሚፈልጉ  ምዕመናን  ቁጥራቸው  ብዙ  ስለሆነ  ሁሉም  አብያተ  ክርስቲያናት  በምዕመናን ይጨናነቃሉ፡፡  እግዚአብሔር  አብ ቤተክርስቲያን  ሴቶቹን  ውጪ  አውደ  ምሕረቱ  ላይ  በመውጣት  ካህናት  ቅዱስ  ቁርባን  ያቆርቡዋቸዋል፡፡ 

    ግሸን  አምባ  መካከል  ላይ  ከኢየሩሳሌም  በመጣው  የዮርዳኖስ  ውሃ  አምሳል  መካከለኛ  ኩሬ  ይገኛል፡፡  በበዓሉ  ላይ  እንደጠበል  ያገለግላል፡፡ 

    ማጠቃለያ፡ - 
    የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ  ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያን  እጅግ  ብዙ  የሆኑ  ቅዱሳት  መካናት  ውስጥ  አንዷ  ግሸን  ማርያም  በመሆንዋ  ምዕመናን  ታሪካቸውን  ከማወቅ  ብሎም  ተባርኮ  ከመምጣት  ባሻገር  ለንግስ  ሲሄዱ  በአለባበስ  ሥርዓት  ቢጠብቁ  በየቦታው  ቆሻሻ  ጥሎ  ውቧን  አምባ  ከማበላሸት  እንዲቆጠቡ  የሄዱበትን  ዓላማ  ሳይረሱ  እየጸለዩ፣  ውዳሴዋን  ቅዳሴዋን  እየሰሙ  ጠበሉን  ጠጥተው  መስቀሉን  ተሻሽተው  ስጋ  ወደሙን  ተቀብለው  በበረከት  መመለስ  አለባቸው:::

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ንግሥት እሌኒና የመስቀሉ ታሪክ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top