• በቅርብ የተጻፉ

    Sunday 18 October 2015

    ቅዱሳን ሐዋርያት ክፍል ፪

    የሐዋርያት ዝርዝር
    በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሐዋርያት ዝርዝር በአራት ቦታዎች ተጽፎ ይገኛል፡፡ እነዚህ ዝርዝሮች በማቴዎስ፣ በማርቆስና በሉቃስ ወንጌሎች ሲገኙ በዮሐንስ ወንጌል ግን ዝርዝሩ አልሠፈረም፡፡ የመጨረሻው ዝርዝር የሚገኘው በሐዋርያት ሥራ ላይ ነው፡፡ በማቴዎስ 10.1-4፣ እንደሚከተለው ዘርዝሯቸዋል

    ጴጥሮስ
    እንድርያስ
    ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
    ፊልጶስ
    ዮሐንስ
    በርተሎሜዎስ
    ቶማስ
    ማቴዎስ
    ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ
    ስምዖን ቀነናዊ
    የያዕቆብ ይሁዳ
    ያስቆሮቱ ይሁዳ

    ይህ የሐዋርያት ዝርዝር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን አዋልድ መጻሕፍትም በልዩ ልዩ ቦታ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ ያህልም የገድለ ሐዋርያትንና የቅዳሴ ማርያምን መመልከት ይቻላል፡፡

    ከ12 ሐዋርያት መካከል ጴጥሮስ፣ ዮሐንስ ያዕቆብ፣ እንድርያስ፣ ቶማስ፣ ማቴዎስ፣ ስምዖን ቀነናዊ፣ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ፣ በርተሎሜዎስና ፊልጶስ በአራቱ የመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ዝርዝሮችና በሁለቱ አዋልድ መጻሕፍት ላይ ስማቸው ሳይለወጥ የሚገኝ ሲሆን ያስቆሮቱ ይሁዳ ደግሞ ታንቆ በመሞቱ የተነሣ በሐዋርያት ሥራ ላይ ስሙ ባይጠቀስም በሦስቱ ወንጌላውያን መጻሕፍትና በገድለ ሐዋርያት ላይ ተጽፎአል፡፡
    ሐዋርያው ማትያስ የተተካው በዚሁ ሐዋርያ ምትክ ነው፡፡ በቅዳሴ ማርያም ላይም አባሕርያቆስ ስሙን ጠቅሶት ይገኛል፡፡
    ታዴዎስ ከአራቱ የመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ዝርዝሮች በሁለቱ እና በሁለቱ አዋልድ መጻሕፍት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ የያዕቆብ ይሁዳ (ከአስቆሮቱ ይሁዳ ለመለየት) ደግሞ በቀሩት ሁለቱ ማለትም በሉቃስ ወንጌልና  በሐዋርያት ሥራ ላይ ተመዝግቦአል፡፡

    ማቴዎስና ማርቆስ እንዲሁም ገድለ ሐዋርያትና ቅዳሴ ማርያም ታዴዎስ በሚለው ስሙ ሲጠሩት ወንጌላዊው ሉቃስ ግን በሁለቱም መጻሕፍቱ (በወንጌሉና በየሐዋርያት ሥራ) ‹የያዕቆብ ይሁዳ፣ የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ›፣ በማለት ይጠቅሰዋል፡፡
    በእሥራኤላውያን ዘንድ ከአንድ በላይ ስም የተለመደ ነው፡፡  ምክንያቱም ከብዙ ሕዝብ ጋር በመኖራቸውና የብዙ ቋንቋ ማለትም የግሪክ፣ የዕብራይስጥ፣ የአራማይክ፣ የሮማይስጥ ወዘተ. ተናጋሪዎች በመሆናቸው በልዩ ልዩ ቋንቋ ብዙ ስሞች አሏቸው፡፡
    ለምሳሌ
            ጴጥሮስ (ላቲን) ፤ ስምዖን (ዕብራይስጥ) ፤ ኬፋ (አራማይክ)
            ቶማስ (ዕብራ) ፤ ዲዲሞስ (በግሪክ   መንታ ማለት ነው፡፡)
            ማቴዎስ - ሌዊ
            ማርቆስ - (ሮማይስጥ)፣ ዮሐንስ (ዕብራ)
            ሳውል (ዕብራ)፣ ጳውሎስ (ግሪክ)
    በልዩ ልዩ ስም ተጠርተዋል፡፡ በዚህም መሠረት ታዴዎስም ‹ልብድዮስ-የያዕቆብ ይሁዳ› ተብሎ በሦስት ስም ተጠርቷል፡፡

    የሐዋርያት ክብር በቤተ ክርስቲያን

    ቅዱሳን ሐዋርያት የቤተ ክርስቲያን ቀዳማውያን አበው፣ ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሠው፣ ሕይወታቸውን ለቤተ ክርስቲያን የሰጡ፣ በመሆናቸው በቤተ ክርስቲያን ዘንድ ልዩ ክብር አላቸው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በልዩ ልዩ መንገድ ታከብራቸዋለች፡፡

    ሀ. ትምህርታቸውን ሳታዛባ በመጠበቅ፡- በዙዎች በልዩ ልዩ ዘመን ከእውነተኛው ትምህርተ ሐዋርየት አፈንግጠዋል፡፡ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በሲሞን መሠርይ መሥራችነት ከተነሱት ግኖስቲኮች ጀምሮ በኋላ ዘመን እስከፈለቁት አርዮሳውያን፣ መቅዶንዮሳውያን፣ ሰባልዮሳውያን፣ ንስጥሮሳውያን፣ መሐመዳውያንና ሉተራውያን ድረስ ሐዋርያዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያቆየችላቸውን ትምህርተ ሐዋርያት፣ ትውፊት ሐዋርያትን ትተው በገዛ ፍልስፍናቸውና ምኞታቸው ፈቃድ ሲመሩ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን የሐዋርያትን ትምህርትና ትውፊት ጠብቃ እስከዛሬ ኑራለች፡፡

    ለ. ገድላቸውን በመመስከር፡- አበው ሐዋርያት የክርስትና ኑሮ ፋና ወጊዎች በመሆናቸው ከከሀድያን፣ ከመናፍቃን፣ ከአረማውያን፣ ከትዕቢተኛ መኳንንትና

    መሳፍንት፣ ከዚህ ዓለም የዲያብሎስ አሽከላ ጋር ተጋድለው በደማቸው ቀለም በአጥንታቸው ብዕር ነው - ክርስትናን የጻፉት፡፡ ጽፈውም ብቻ ሳይሆን ኑረው ቀምሰው አሳይተውናል፡፡ ‹እግዚአብሔር ቸር እንደሆነ  ቅመሱ እዩም› እንዳለ ልበ አምላክ ዳዊት
    በሹክሹክታ የተማሩትን በጩኸት፣ በጨለማ የተማሩትን በብርሃን፣ በቤት የተማሩትን በሰገነት ገልጠውታል፡፡ በዚህ ጊዜም ጨለማ የሰፈነበት ዓለም የወንጌልን ብርሃን መቀበል ተስኖት ፍዳ መከራ አብዝቶባቸዋል፡፡ ይህ ያደረጉት ተጋድሎ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ በገድላቸው፣ ወዘተ ይገኛል፡፡ ጽፎ መረከብ ማስተማርም ብቻ ሳይሆን በእግራቸው የተተኩ አበውም መንገዳቸውን ተከትለውታል፡፡
    ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያትን ተጋድሎ ለትውልድ ሁሉ ትመሰክረዋለች፡፡ ልጆቿ አሠረ ፍኖታቸውን እንዲከተሉ ታስተምራቸዋለች፡፡ ልጆቿም ‹የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፡፡  ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእሥራትና በወኅኒ ተፈተኑ፡፡ በመጋዝ ተሠነጠቁ፡፡ በሠይፍ ተገድለው ሞቱ፡፡ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፡፡ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፣ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ፡፡› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ ዕብራ. 11.38፡፡
    ስለ ወንጌል ክብር፣ ስለ ርትዕት ሃይማኖት የተሠው፣ የቤተ ክርስቲያን መዓዛ የሆኑ ሐዋርያትን ገድል በተግባር ያውሉታል፡፡

    ሐ. በዓላቸውን በማክበር፡- ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ሐዋርያት የሰማዕትነታቸውን (ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር፣ እርሱ ግን ሳይሞት ወደ

    ብሔረሕያዋን ስለተወሰደ የተወለደበት ይከበራል፡፡ ዮሐ. 21.22፡፡) በዓል ታከብራለች፡፡ የጻድቅ ሞቱ በእግዚአብሔር ዘንድ የተከበረ ነውና፡፡

    ይህ የሐዋርያት በዓል ከመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ጀምሮ ይከበር ነበር፡፡ የሰርምኔሱ ሊቀ ጳጳስ ፖሊካርፐስ ሐዋርያት በሰማዕትነት ያረፉበት በዓል በጥንታውያን ክርስቲያኖች ዘንድ ይከበር እንደነበር በ2ኛው መ/ክ/ዘመን ላይ ዘግቦ ነበር፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሐዋርያት በዓል በድምቀት በቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የበዓላት ቀኖና መሠረት የቅዱሳን ሐዋርያት በዓል የሚከበርበት ዕለት እንደሚከተለው ነው፡፡

    1. ዮሐንስ ወንጌላዊ ...... መስከረም 4 (ልደቱ)
    2. ሐዋርያው ማቴዎስ...... ጥቅምት 12
    3. ሐዋርያው ፊልጶስ ........ ኅዳር 18
    4. ሐዋርያው እንድርያው...... ታኅሳስ 4
    5. ሐዋርያው ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ........ የካቲት 10
    6. ሐዋርያው ማትያስ....... መጋቢት 8
    7. ሐዋርያው ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ....... ሚያዝያ 17
    8. ሐዋርያው በርተሎሜዎስ....... መስከረም 1
    9. ሐዋርያው ስምዖንን ቀነናዊ/ናትናኤል........... ግንቦት 15
    10. ሐዋርያው ቶማስ......... ግንቦት 26
    11. ሐዋርያው ታዴዎስ......... ሐምሌ 2
    12. ሐዋርያው ጴጥሮስ......... ሐምሌ 5
    13. ሐዋርያው ጳውሎስ ......... ሐምሌ 5

    መ. በስማቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በመሰየም:-አስቀድሞ እግዚአብሔር በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል ‹ሰንበቴን ስለሚጠብቁ፣ ደስ የሚያሰኘኝንም ነገር ስለሚመርጡ፣

    ቃል ኪዳኔንም ስለሚይዙ ጃንደረቦች እንዲህ ይላል፡- በቤቴና በቅጥር ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋለሁ› ኢሳ. 56.4 ብሎ ለቅዱሳን ልጆቹ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ታቦት ተቀርፆላቸው በስማቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ይከበራሉ፡፡
    ሠ. በስማቸው በመጠራት፡-  ቅዱሳን ሐዋርያት የቤተ ክርስቲያን መሠረት የክርስትና ፈር ቀዳጅ ናቸውና ዘወትር ሊታሰቡ ይገባል፡፡ በመሆኑም በክርስቲያኖች ዘንድ ክርስትና ከተነሱበት ዕለት ጀምሮ በስማቸው መጠራት ባህላችን ነው፡፡

    ረ. ሥዕላቸውን በማክበር ፡- ከጥንቱ የካታኮምብ (ግበበምድር) ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ የቅዱሳን ሐዋርያት ሥዕል ለሥርዓተ አምልኮ (ለጸሎት፣ ለምልጃና ለምሥጋና) መጠቀም የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ነው፡፡ ከዚያም በኋላ እስከ ዛሬ ድረስ የሐዋርያት ሥዕል በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑ ይገኛል፡፡ ምእመናንም አስቀድመው የልብሳቸውን ዘርፍ እየነኩ በጥላቸው ላይ እየተኙ ይፈወሱ እንደነበሩት ሁሉ የሐዋ. 5.15፣ 19.11 ዛሬም ሥዕላቸውን እየዳሰሱ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ ያገኙበታል፡፡

    ሰ. በአማላጅነታቸው በመታመን ፡- የቅዱሳን አማላጅነት  በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርትና በቤተ ክርስቲያን ታሪክ በተለያዩ ቦታዎች ተገልጦ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት የቅዱሳን ሐዋርያት አማላጅነትም ከመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ጀምሮ

    የታወቀ የታመነም ነው፡፡ በሮማ መንግሥት ጨካኝነት የተነሣ በግበበምድር ለመኖር የተገደዱት ጥንታውያን ክርስቲያኖች፣ በግበበ ምድሩ ግድግዳ ላይ በጻፉት ጸሎታቸው፤‹ጳውሎስና ጴጥሮስ ሆይ ድል እናገኝ ዘንድ ጸልዩልን› ብለው የተናገሩት ተገኝቷል›፣፣

    ዋቢ ፡ ቤተክርስቲያንህን ዕወቅ መጽሐፍ
           ፣ ዜና ሐዋርያት

                                                              

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ቅዱሳን ሐዋርያት ክፍል ፪ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top