• በቅርብ የተጻፉ

    Tuesday 27 October 2015

    ጥቅምት 27

    "እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም፡ ወገብረ መድኃኒተ በማዕከለ ምድር"
    እግዚአብሔር ዓለም ሳይፈጠር የነበረ የዘለዓለም ንጉሥ ነው፤ በማዕከለ ምድር ቀራንዮ ኢየሩሳሌም ተሰቅሎ ባፈሰሰው ደሙ መድኃኒትን አደረገ ይላል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት /መዝ. 73፡12/ 

    ይህ በመጋቢትና በጥቅምት 27 ቀን በየዓመቱ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት የምናከብረው በዓላችን ዓመተ ፍዳው፤ ዓመተ ኲነኔው አክትሞ የሰው ዘር የሆነው ሁሉ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከኃጢአት ወደ ስርየት፣ ከሲኦል ወደገነት፣ የተመለሰበትና የተሸጋገረበት ዕለት መሆኑን ለማዘከር ነው፡፡ አዳም በሥላሴ አርአያና አምሳል ተፈጥሮ ጸጋ እግዚአብሔርን ተጎናጽፎ ነጻ የኅሊና ፈቃድ ያለው ሰው ሁሉ ገነትን ያህል ቦታ ይዞ ሥዩመ እግዚአብሔር፡ ነቢየ እግዚአብሔር፣ ካህነ እግዚአብሔር ሁኖ ለሰባት ዓመታት በስነ ሥርዓት በገነት ይኖር ነበር፣ ይሁንና እግዚአብሔር ያደረገውን ሁሉ አየ፤ እነሆም እጅግ መልካም ሆነ /ዘፍ. 1፡31/ ከሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እንደምንረዳው እግዚአብሔር አምላካችን በስድስቱ ቀናት የፈጠረው ሁሉ መልካም ሲሆን በተለይም በሥላሴ አርአያና አምሳል ለተፈጠረው ሰው የሕይወት እስትንፋስን ሰጥቶ በገነት በሕያውነት እንዲኖር ያስቀመጠው የከበረ ክቡር ፍጡር ነበር፡፡ "ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ ይላል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት፡፡

    እግዚአብሔር የሰውን ልጅ የስሙ ቀዳሽ የክብሩ ወራሽ አድርጎ ቢፈጥረውና የጸጋ ገዥ ቢያደርገው ያልተሰጠውን የባህርይ አምላክነትን በመፈለጉ የገዥና የተገዥ፣ የፈጣሪና የፍጡር መለያ የሆነውን ትእዛዘ እግዚአብሔርን በመጣሱ በዚህ ምክንያት ሞተሥጋ፣ ሞተ ነፍስ ተፈረደበት፡፡ ከክብሩ ተዋርዶ ከገነት እንዲወጣ ተደረገ፡፡ ተመልሶ ወደገነት ገብቶ ተጨማሪ ኃጢአትን እንዳይሠራም ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውን መንገድ ለመጠበቅ የምትገለባበጥ የነበልባል ሰይፍ ሜሎስን በእጃቸው የያዙ ኪሩቤልን በኤደን ገነት ምሥራቅ አስቀመጠ ይላል የሙሴ መጽሐፍ፡፡ /ዘፍ. 3፡22-24/

    አዳም ሳይቸገር በጠላት ከንቱ ስብከት እንደእግዚአብሔር ለመሆን ክፉውንና ደጉንም ፈጥኖ ለማወቅ ቸኩሎ ትእዛዘ እግዚአብሔርን በማፍረሱ ወደቀ፣ አወዳደቁም ታላቅ ሆነ፡፡ በሰው ሕይወት ላይ አሳፋሪ፣ አስፈሪና አስነዋሪ ታሪክ ፈጸመ፡፡ አዳም እግዚአብሔር አታድርግ ያለውን የአምላኩን ትእዛዝ በማፍረስ የሞተ ሞት ተፈረደበት፡፡ ከዚህ አሳፋሪና አስፈሪ ታሪክ በመነሣት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስለሞት ማሰብ ለማንም ሰው ቢሆን ቀላል ነገር አልሆነም፡፡ ያ ሰው የኖረው ሞተ ሥጋና ሞተ ነፍስ የሁሉ እድል ፈንታ በሆነበት ጊዜ ነበርና ነው፡፡መጽሐፍ ቅዱስ ለሰዎች አንድ ጊዜ መሞተ ከእርሱ በኋላ ፍርድ ተመደበባቸው ይላል፡፡ ዕብ. 9፡27

    ነቢዩ ሕዝቅኤልም እነሆ ነፍሳት ሁሉ የእኔ ናቸው፣ የአባት ነፍስ የእኔ እንደሆነች፣ ደግሞ የልጅ ነፍስ የእኔ ናት፣ ኃጢአትየምትሠራ ነፍስ እርሷ ትሞታለች፡፡ /ሕዝ. 18፡4/ በማለት የዚህን ማስጠንቀቂያ፣ ኃይለኛነትና ጥብቅነት ያሳያል፡፡ በቀል የእኔ ነው እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና ደግሞም ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል፣ በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅም የሚያስፈራ ነው ያላል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ /ዕብ. 10፡30-31/፡፡

    ስለዚህ፣ ሞት፣ የኃጢአት ዋጋ ሆኖ በኃጢአት ምክንያት የመጣ ቢሆንም በኃጢአት ላይ የተሰጠ የመጨረሻ ፍርድ /ቅጣት/ ባለመሆኑ ከሞት በኋላ ሌላ ፍርድ የሚጠበቀን መሆኑን ያስተምረናል፡፡ ይሁንና ቀዳማዊ አዳም በስህተቱ ተጸጽቶ በማዘኑ፣ በማልቀሱና ንስሐ በመግባቱ ለቸርነቱ ወሰን የሌለው አምላክ ንስሐውን ተቀብሎ የተስፋ ቃል ሰጠው፡፡ የተሰጠውም የተስፋ ቃል አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ሥጋዬን ቆርሼ ደሜን አፍስሼ አድንኅለሁ የሚል ነበር፡፡ ይህ የተስፋ ቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ፣ ትንቢት ሲነገር ሱባኤ ሲቆጠር ኖሮ አምስት ሺህ አምስት መቶ የተስፋው ዘመን ሲፈጸም የተናገረውን የማይረሳ፣ የሰጠውን ተስፋ የማይነሣ እግዚአብሔር "ክርስቶስኒ መጽአ በዕድሜሁ ይሙት በእንተ ኃጢአትነ እንዘ ኅጥአን ንሕነ" /ሮሜ. 5፡6/ ይላል ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ጊዜው ሲደርስ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሰው ልጅ ኃጢአት ሊሞትመጣ፣ ሰው ሆነ በሥጋም ተወለደ፣ በተወለደ በ30 ዘመኑ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠመቀ፣ ዕለቱን ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ዓርባ መዓልትና ዓርባ ሌሊት ጾመ፣ በሰይጣን ተፈተነ፣ ፈታኙ ሰይጣንም ባቀረበው ፈተና ድል ተመታ፣፣

    ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራውን የጀመረው በጥምቀት፣ በጾም በጸሎት በትምህርት በተአምራት ሲሆን ሦስት ዓመታት ከሦስት ወራት በይሁዳ፣ በሰማርያና በገሊላ አውራጃዎች በቅድስት ሀገር እየተዘዋወረ ወንጌልን አስተማረ፡፡ ትምህርቱ እየሰፋና እየተዳረሰ ሲሔድ የተነገረውን ትንቢት ለመፈጸም ለሕማም፣ ለሞት፣ በክብር ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ ተሰቀለ፣ በሥጋ ሞተ፣ ተቀበረ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ውሎና አድሮ ከሙታን ተለይቶ በመነሣት ሞትን ድል አደረገ፡፡

    ስለሞተ ነፍስና ሞተ ሥጋ ብዙ ተብሏል፣ እየተባለም ነው፣ እነዚህ ሁለቱም በመጀመሪያው ሰው፣ ሕግ ተላላፊነት በአንድ ወቅት በሰው ሕይወት ላይ የደረሱ አሳዛኝ ድርጊቶች ናቸው፡፡ ቀደም ሲል ለማለት እንደሞከርነው በመጀመሪያው ሰው ሕግ ተላላፊነት ሞተ ነፍስና ሞተ ሥጋ በዚህ አጋጣሚ ሁለቱም በዚያን ጊዜተያየዘው የመጡ ሲሆን ሞተ ነፍስ በ34 ዓ.ም በማዕከለ ምድር ቀራንዮ በስግው ቃል ሞተ ሥጋ አክትሞለት ሁሉም የአዳም ልጅ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከኃጢአት ወደ ስርየት፣ ከሲኦል ወደ ገነት ተመልሷል፣ ይሁንና ሞተ ሥጋው የክርስቶስን ዳግም ምጽአት ትንሣኤ ዘጉባኤን በመጠበቅ ላይ ይገኛል፡፡ በዚያን ጊዜ ሞተ ሥጋውም ያከትምለታል፡፡ በዚያን ጊዜ በማዕከለ ምድር ቀራንዮ፣ ክርስቶስ ከተሰቀለበት መስቀል አናት ኢየሱስ ናዝራዊ ንጉሠ አይሁድ የሚል በእብራይስጥ በፅርዕና የሮማይስጥ ተጽፎና ተለጥፎ ይነበብ ነበር፡፡ የእነዚህ የሦስቱ መንግሥታት የሥልጣን፣ የሥልጣኔና የጥበብ ኃይል በአንድነት ቢተባበሩም የክርስቶስን ኃይል ሊቋቋሙት አለመቻላቸው በግልፅ ታይቷል፡፡

    ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሞት መደምሰሻ፣ የሰይጣን ድል መንሻ፣ የድኅነት ጋሻ ያደረገው መስቀል በክርስትና ሕይወት የላቀ ክብርና ቦታ ያለው ሆነ፡፡ሰውን በስቅላት መቅጣት የተጀመረው የፋርስ ባቢሎን እንደነበረ በታሪክ የሚታወቅ ሲሆን መስቀል ከዘመነ ሥጋዌ በፊት የወንጀለኞች፣ የኃጢአተኞችና የበደለኞች መቅጫ መሣሪያ መሆኑ የታወቀ ነበር፡፡ ጌታ በዚህ ዓለም በተገለጠበት ጊዜ በዓለም ግዛቱን አስፍቶና አስፋፍቶ የነበረው የሮሜው የቴሣሩ መንግሥት ይህን የስቅላት አሠራር ልምድ ከፋርስ ባቢሎን ወርሶ ምንም ዓይነት ኃጢአት ሳይኖርበት በኃጢአተኞች ይሙት በቃ የተፈረደበት ጌታችን፣ አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመሰቀልላይ ተሰቅሎ እንዲሞት ፍርድን ሰጠ፡፡

    ቅድስት ድንግል ማርያምን ከገሊላ አውራጃ ከናዝሬት ወደ ይሁዳ አውራጃ ወደ ዳዊት ከተማ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ የወሰዳት የሮማዊው የአውግስጦስ ቄሣር የሕዝብ ቆጠራ ትእዛዝ ሲሆን /ሉቃ. 2፡1-3/ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለውም የክርስቶስ ስቅላት የተካተተውም ሮማዊው እንደራሴ ጲላጦስ በሰጠው ትእዛዝና ፍርድ ነበር፤ ይሁንና እኛ ጲላጦስን ጻድቅ ሰው አርገን ይዘነዋል፡፡ የሮሜ ዜግነት የነበረው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በሌላ ቦታ ያለ አግባብ የተፈረደበትን እንዲያይለት ወደሮሜው ቄሣር ይግባኝቢልም ቄሣር ከጊዜ በኋላ የይሙት ፍርዱን አጽድቆ በሮማውያን አደባባ በሰይፍ እንዲገደል አድርጎታል፡፡ /የሐዋ. 25፡11-13/

    ከዚህ አንጻር የሮማውያን ሕግ አዋቂነትና አስከባሪነት ደካማ፣ የአይሁድ ሃይማኖታዊ ሥርዓትም ከሁሉም አቅጣጫ የተራቆተ የግሪኮችም ፍልስፍና ከንቱ መሆኑን እንመለከታለን፡፡ እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ሦስት ኃይላትም አቋማቸውን አጠናክረው በኃይላቸው ተመክተው ለጊዜው የሚያሸንፉ መስለው ቢነሡም ከጊዜ በኋላ ሁሉም ፈርሰውና ወድመው ሲቀሩ ክርስቶስ ግን በሚወዱትና በሚያፈቅሩት ተከታዮቹ ልብ ለዘለዓለም የማይፈርስ ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን መሥርቷል፡፡ ይህም ወንጌለ መንግሥተ ሰማያት እስከዓለም ፍጻሜ ሲሰበክ ይኖራል፡፡

    ከመጋቢት 27 ቀን 34 ዓ.ም ጀምሮ መስቀል የነፃነት አዋጅ የተነገረበት ሰላማዊ ዙፋን ስለሆነ ለክርስቲያኖች ሁሉ የድልና የአርነት፣ የፍቅርና የሰላም ምልክት ሆነ፡፡ከዘመነ ሰማዕታት በኋላ በዐራተኛው መቶ ዓመት የተነሣው የቢዘንታይን ንጉሠ ነገሥት ታላቁ ቆስጠንጢኖስ በዝንቱ ትእምርተ መስቀል ትመው ፀረከ በሚል በብርሃን ቅርፅ ያየው መስቀል የድል ምልክት ሆኖ ይኖራል፡፡ቀደም ሲል በተመሳሳይ እንደተጠቀሰው ሐዋርያት ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረው ቃል መስቀል የእግዚአብሔር የማዳን ኃይል የተገለፀበትና የሚገለፅበት መሣሪያ መሆኑን ያስረዳል፡፡" እስመ ነገረ መስቀሉስ ዕበድ ውእቱ በኀበ ኅጉላን ወበኅቤነሰ ለእለ ድኅነ ኃይለ እግዚአብሔር ውእቱ" የመስቀሉ ቃል ወይንም የመስቀሉ ነገር ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድነው ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና ይላል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ /1ኛ ቆሮ. 1፡18/ የመስቀሉ ነገር ሞኝነትና ኃይል በሆነላቸው ሰዎች መካከል እንደመለኪያና መለያ ያለ ነገር ይሆናል ማለት ነው፡፡ለአይሁድ የመርገም፣ ለአማልክት አምላኪዎች የሞኝነት፣ ለክርስቶስ ቤተ ሰቦች /ወገኖች/ የእግዚአብሔር ኃይል የሆነውን የመስቀሉን ትርጉም ለማስተማር ነው፡፡

    ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ቆሮንቶስ ድረስ ለሁለት ለሦስት ጊዜያት ረጅም ሐዋርያዊ ጉዞ ያደረገው፡፡መስቀል በብሉይ ኪዳን፣ ምሳሌነት የነበረው ሲሆን ይህም የኖኅ መርከብ የተሠራችበት እንጨት፣ ሙሴ የፈርዖንን መሰግላን ድል ያደረገበት በትረ ሙሴ የመስቀል ምሳሌዎች መሆናቸው ይነገራል፡፡ ምእመናን በክርስቶስ አምነው በመስቀል አማትበው ከማየ ደምሳሴ ኃጢአት፣ ከአምልኮተ ጣዖት ድነዋል፣ በመስቀለ ክርስቶስ አጋንንትን፣ መናፍቃንን፣ ፍትወታት እኩያትን ድል ሲያደርጉ ይኖራሉ፡፡ከዚህም የተነሣ የክርስትናው ኪነ ጥበባት ሁሉ ምልክቱ መስቀል ሆኗል፣ ኃይለ እግዚአብሔር የሆነው የመስቀሉ ታሪክ የተመሠረተበት መጋቢት 27 ቀን 34 ዓ.ም በማዕከለ ምድር ቀራንዮ ነው፡፡

    እግዚአብሔርስ ንጉሥ ውእቱ እመቅድመ ዓለም፣ ወገብረ መድኃኒቲተ በማዕከለ ምድር ... እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፣ በምድር መካከልም መድኃኒትን አደረገ በማለት ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የዘመረውንም በመነሻው አሰምተናል /መዝ. 73፡12/፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ማዕከለ ምድር ያለው ቀራንዮ ጎልጎታን ነው፡፡ የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀሉና የመቃብሩ ቦታ ቀራንዮ ጎልጎታ መባሉ ነው፡፡ ይህም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጋቢት 27 ቀን 34 ዓ.ም በዕለተ ዓርብ በዕፀ መስቀል፣ በሥጋ የተሰቀለበት፣ በሥጋ የሞተበትና የተቀበረበት፣ በይቀጥላልም ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ውሎና አድሮ መጋቢት 29 ቀን 34 ዓ.ም በዕለተ እሑድ የተነሣበት ነው፡፡

    የክርስቶስ ቅዱስ መስቀል መጋቢት 27 ቀን 34 ዓ.ም በዕለተ ዓርብ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ድል የተነሣበት ሆነ፡፡ እንኳን አማናዊው የክርስቶስ መስቀል ይቅርና የእርሱ ምሳሌ የሆነው፣ ሙሴ ከእግዚአብሔር መመሪያን ተቀብሎ በምድረ በዳ የሰቀለው አርዌ ብርት እንኳ ሳይቀር ብዙ ተአምራትን ሠርቷል፡፡ እባብ የነደፈው እስራኤላዊ ሁሉ በዓላማ ላይ የተሰቀለውን የናሱን እባብ በእምነት በተመለከተ ጊዜ ሕይወቱን አግኝቷል፡፡ ከደዌው ተፈውሷል፣ ከኀዘኑ ተጽናንቷል /ዘኁቁ. 21፡6-9/ ይህን ያህል ተአምር የሠራው ይህ የመስቀለ ክርስቶስ ምሳሌ የነበረው ነው፣፡

    ይሁንና ከላይ ከተጠቀሰው ዕለትና ዓመተ ምሕረት ወዲህ መስቀል የተፈተነ መድኃኒት በመሆኑ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በመስቀሉ ይመካል፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም የተሰቀልኩበት ከጌታችን ከአምላካችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ ይላል /ገላትያ. 6፡14/፡፡ ይህ ከዚህ በላይ የሰማነው ትምህርት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በስህተት ትምህርት ለተወናበዱት የገላትያ ሰዎች ትክክለኛውን የክርስትና እምነትና ሕይወት ለማሳወቅ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡

    እኛም ስለነገረ መስቀሉ መናገር ያለብን በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎስ ዘይቤ መሆን አለበት፡፡ዛሬ የምናከብረው ዓመታዊ በዐላችን ዓለም ሁሉ ክብር ያገኘበትና ከግብርናተ ዲያብሎስ ነጻ የወጣበት ስለሆነ ይህን የመንፈስ ነጻነት በዐል ስናከብር የሚሰማን ደስታ ከፍተኛ ነው፡፡ቃለ እግዚአብሔር ወልድ በገሊላ አውራጃ በናዝሬት ከተማ ሰው ሆኖ ከቅድስት ድንግል ማርያም በይሁዳ አውራጃ በዳዊት ከተማ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተወልዶ እስከ ማዕከለ ምድር ቀራንዮ፣ ጎልጎታ መስቀል አደባባይ የደረሰበትን መከራ ስንመለከት ሕማማተ መስቀሉን ተቀብሎ፣ ተሰቅሎ፣ ሞቶ ተነሥቶ ሰውን ያዳነበት ዕለት መሆኑን እንረዳለን፡፡

    ከፅንሰት ከልደት ከጥምቀት ከትምህርት አሰጣጡ ከተአምራቱ ድርጊት ሒደት አንሥቶ እስከ ቀራንዮ ጎልጎታ ድረስ በመጨረሻም በመስቀል ላይ ሆኖ ወይቤ ተፈጸመ ኩሉ ብሎ የአዳምን የክብሩን ፍጻሜ በመስቀሉና በትንሣኤው እስከ አጠቃለለው ድረስ የተቀበለውእያንዳንዱ ጸዋትወ መከራ የሰውን ክቡርነት፣ መንፈሳዊ ሕይወት ልዕልና የሚገልጽ ነው፡፡ከላይ እንደተጠቀሰው ቀዳማዊ አዳም የአምላኩን ትእዛዝ በማፍረሱ ምክንያት ከአንዲት የበለስ ቅንጣት በፈሰሰው ደም በተፈጥሮውንጹሕ የነበረው የሰው ሕይወት በኃጢአት አድፎ እንዳይቀር የዚህን አጸፋ የሚመልስ መከራ ተቀብሎ ባፈሰሰው ደሙ የአዳምን ፍዳለማስወገድና ወደ ቀደመው ክብሩ ለመመለስ ስለሰው ሕይወት ብሎ በፍርድ አደባባይ መቆምና መወቀስ፣ መገረፍ፣ መውደቅ፣ መነሣት፣ መጸፋትና መመታት፣ መስቀልን ተሸክሞ መጓዝን መገፋት፣ መራራ ሐሞትን ለጥማቱ መቀበል ይህን ሁሉ በእኛ በፍጡራን ደረጃ ስንመለከተው ከሰው ትዕግሥትና ችሎታ በላይ መሆኑን እንረዳለን፡፡

    ሰለሆነም ከዚህ በላይ የተጠቀሰውን መከራና ስቃይ ከተቀበለ በኋላ ዓርብ መጋቢት 27 ቀን 34 ዓ.ም በዕለተ ዓርብ በማዕከለ ምድር ቀራንዮ አኅዜ ዓለም የሆነ እጁን በመስቀል ላይ ዘርግቶ በፈቃዱ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ፡፡ መለኮት በአካለ ነፍስ ወደሲኦል ወርዶ በአዳምና በሔዋን፣ በልጆቹ ሁሉ ስም ተጽፎ የነበረውን ስመ ተዋርዶ አጥፍቶ በሲኦል ተግዘው የነበሩትን ነፍሳት ነጻ አውጥቶ ገነትን አወረሳቸው፡፡ ስለዚህ ይህ በዓላችን የሰው ፍጹም ክብሩ የተመለሰበት፣ የሞትና የኃጢአት እንዲሁም የዲያብሎስ ሥልጣን የወደቀበትና የተሻረበት ቀን ስለሆነ ዓለም ሁሉ ትንሣኤ ዘለክብርን ወደሚያድለው ወደ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንቃዕደወ ልቡና ዕደ ኅሊናውን ሰቅሎ ምስጋና ማቅረብ ይገባዋል፡፡እስከዚህ የተገለፀው ዛሬ መታሰቢያነቱን የምናከብረው በዓላችን የሰው ልጆች አባት የሆነው ቀዳማዊ አዳም በዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ፍርድ ወደ ዘለዓለማዊ ሕይወት የተመለሰበት፤ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዳዊት ከተማ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ ልደቱ ጀምሮ እስከ ቀራንዮ ጎልጎታ ድረስ ለሰው ልጅ ያደረገውን ቸርነት የምናዘክርበት፤ ከጌታችን ከአምላካችን ከመድኃኒችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው የተሰጠ የደኅነት ጸጋ የተረጋገጠበት፤በዓለም ሁሉ ሰላም የወረደበትና ፍጡር ከፈጣሪው ፍጹም ሕይወትን ያገኘበት ዕለት ነው ብለን ነው፡፡

    ስለዚህ ይህ ዕለት የሰላማችን፣ የደስታችንና የድል በዓላችን ስለሆነ በየዓመቱ በዝማሬ፣ በውዳሴና በቅዳሴ እናከብረዋለን፡፡ከዚህ ዕለት አድርሶ በዓላችንን ለማክበር እንዳበቃን ለሚመጣውም 2009 ዓ.ም አድርሶ ለማክበር እንዲያበቃን የእግዚአብሔር አምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

    እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታችንን፣ ድካማችንን ተቀብሎ ምሕረቱን፣ ቸርነቱን ያድርግልን፡፡እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን ይስጥልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ይባርከን ይቀድሰን!

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ጥቅምት 27 Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top