• በቅርብ የተጻፉ

    Wednesday 11 November 2015

    ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል


    እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል አመታዊ በዓልአደረሳችሁ።

    ይትዐየን መልአከ እግዚአብሔር ዐውዶሙ ለእለ ይፈርህዎ ወያድኅኖም ጣዕሙ ወታእምሩ ከመኄር እግዚአብሔር። መዝ.33 (34)7-8

    መላእክት የሚለው ቃል መልእክተኞች 'ተላላኪዎች'የእግዚአብሔር ይቅርታ ወደ ሰው የሰውን ልመና ወደእግዚአብሔር የሚያደርሱ' የእግዚአብሔር ልዩ ወዳጆች ማለት ነው፡፡ በሌላ መልኩ አለቆች ገዥዎች ወይም የቤተክርስቲያን አስተዳዳሪዎች ማለት ይሆናል፡፡ ሚካኤል ማለት ‹‹መኑ ከመ እግዚአብሔር 'እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?›› ማለት ነው፡፡ሚካኤል በስም ተለይቶ መጠቀስ የተጀመረው በመጽሐፈ ዳንኤል /ዳን.10፥13' 2፥1/ ውስጥ ነው፡፡በመጽሐፈ ሄኖክም ለበርካታ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ከዚህ ሌላ በብሉይ ኪዳን አዋልድ መጽሐፍት በኪዳነ አብርሃም ውስጥ ተጠቅሶም ይገኛል፡፡

    ቅዱስ ሚካኤል ለፍጥረታት ሁሉ የሚራዳና የሚያዝን የምሕረትና የመዳኛ፤ የሰላም መልአክ ነው፡፡ ‹‹በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል›› /ዳን.12፥1/ በማለት በነቢዩ ዳንኤል የተነገረ ሲሆን በሌላ ቦታ ‹‹ከዋነኞቹአለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ›› /ዳን. 10፥13/ በማለት ያስረዳል፡፡ በዚህ ቃል ላይከዋንኞቹ አለቆች አንዱ የሚለውን በመያዝ ሚካኤል ብቻ የመላእክት አለቃ አይደለም የሚሉ አሉ፡፡ ነገር ግን የሌሎች አለቅነት የተወሰነ ወይም ዝቅተኛ ሲሆን በአንድ ነገድ ላይ በአንድ የመላእክት ከተማ ላይ ነው፡፡የቅዱስ ሚካኤል አለቅነት ግን በመላእክት ሁሉ ላይከሆነ ከሌሎቹ ይለያል፡፡ በድርሳነ ሩፋኤል ላይ እንደተገለጸው ሰባት ሊቃነ መላእክት ቢኖሩም አለቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡

    ቅዱስ ሚካኤል አርምሞ ትዕግሥትን የሚወድ መልአክ ነው፡፡ ‹‹የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር ጌታ ይገሥጽህ አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም›› ቅዱስ ሚካኤልከእግዚአብሔር በተሰጠው ኃይል ዲያብሎስን ድል የነሣ መልአክ ነው፡፡ ‹‹በሰማይ ጦርነት ተነሣሚካኤልና እርሱ መላእክት ከዘንዶው ከመላእክቱም ጋር ተዋጉ›› /ራእ. 12፥7/ ይላል፡፡

    የቅዱስ ሚካኤል በዓል ሰኔ 12 የሚከበርበት ምክንያት ዲያብሎስን በፈቃደ እግዚአብሔር ተዋግቶ ያሸነፈበት አምላክነትን ሽቶ በወደቀው በዲያብሎስምትክ ሊቀ መላእክት ሆኖ የተሾመበት ዕለት በመሆኑነው፡፡ ‹‹ክብር ይግባውና እግዚአብሔር በዚህች ዕለት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ከወገኞቹ ከመላእክት ሁሉ በላይ አክብሮ ሹሞታል›› ይላል ድርሳነ ሚካኤል

    ከዚህ በተጨማሪ ይህ ዕለት ቅዱስ ሚካኤል አፎምያን ያዳነበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ በአንዲት አገር ሃይማኖቱ የቀና ታላቅ መኮንን ከሙ አስተራኒቆስ የሚባል ሰው ነበር፡፡ ሚስቱም አፎምያ ትባላለች፡፡አፎምያ ባልዋ አስተራኒቆስ ታሞ እያለ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል አስሎ እንዲሰጣት ለመነችው፤ እንዳለችው አደረገላትና ባልዋ ሞተ፡፡ከዚህ በኋላ አፎምያ ባልዋ ያሠራላትን ሥዕል ይዛ በሃይማኖት ጻንታ ስትኖር ዲያብሎስ በተለያየ መልኩይፈትናት ጀመር፡፡ አንድ ጊዜ ባልቴት እየመሰለ ሌላጊዜ ሌላ እየሆነ ባል ማግባት እንዳለባት መከራት፡፡መጽሐፍም ጠቀሰላት፡፡ ከንጉሡ ጋር ማጋባት እንዳሰበ ነገራት እርሷ ግን ማግባት እንደማትሻ እግዚአብሔርን እያገለገለች ኖራ ማለፍ እንደምትፈልግ ነገረችው፡፡ ዲያብሎስ ግን ፈተናውን እያባሰ እያባሰ መጣ፡፡ በመጨረሻ ግን በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል አሳፍራ አዋረደችው፡፡

    የሰኔ ሚካኤል ዕለት ዲያብሎስ ዳግመኛ ሊፈትናትመጣ፡፡ ሚካኤል ነኝ አላት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል››/2ቆሮ.11፥13/ እንዳለ በዚህን ዕለት የቀረባት ራሱን ለውጦ የብርሃን መልአክ መስሎ ነበር፡፡ አፎምያ ግን አስተዋይ ስለነበረች ‹‹የብርሃን መልአክ ከሆንክ የመስቀል ምልክት ያለበት በትርህወዴት አለ?›› አለችው፡፡ በኛ በመላእክት ዘንድ የመስቀል ምልክት አይደረግም አላት፡፡ እርሷም ስለተጠራጠረችው የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ልታመጣ ወደ ሥዕል ቤቷ ስትገባ ዘለለና አነቃት፡፡ አፎምያ ጮኸች፤ ቅዱስ ሚካኤልም ፈጥኖ ደርሶ አዳናት ዲያብሎስንም አዋረደላት፡፡

    ዲያብሎስ አፎምያ ያሰበችውን ጸጋ ሆኖ የተሰጣትንኑሮ ትታ በተለየ ዓለም እንድትኖር እንደ መከራት በእኛም ሕይወት እንዲህ ሊያደርግ ይችላል፡፡ በጋብቻወቅት ምንኵስናን እንድናስብ' በዕርቅ ሰዓት ጥላቻ እንዲሰማን' በሰላም ጊዜ ጦርነትን' በጾም ጊዜ ምግብን' በትዕግሥት ጊዜ ቁጣን በመረጋጋት ጊዜ አድመኝነትን በውስጣችን ሊያኖር ይችላል፡፡ ስለዚህ እንደ አፎምያ በእምነትና በምግባር ጸንተን በማስተዋል ልንኖር ይገባል፡፡

    የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትየቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት አይለየን፡፡

    ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

    ምንጭ፡- ሐመር 1995 ግንቦት/ሰኔ

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top