• በቅርብ የተጻፉ

    Friday 6 November 2015

    ኆኅተ ብርሃን


    ከላይ ባየነው መልኩ መጻሕፍት ሁሉ ተባብረው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እውነተኛ ብርሃንነት ይመሠክራሉ፡፡ እርሱን አምላክ ብለን ድንግልን ወላዲተ አምላክ፣ እርሱን ጌታ እርሷን የጌታ እናት፣ እርሱን ጌታ እርሷን እመቤት፣ እርሱን አምላክ ወሰብዕ እርሷን ድንግል ወእም እንደምንለው እርሱን ብርሃን ብለን እርሷን እመ ብርሃን እንላለን፡፡ እንደውም “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” (ዮሐ.8፡12) እንዳለ ቅዱሳኑንም “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ” (ማቴ.5፡14) ብሏልና እርሷንም ብርሃን እንላታለን፡፡ በነገረ ማርያም ትምህርት ቴክታና ጴጥርቃ ስለተባሉ ከእመቤታችን ወደኋላ 7 ዘር ስንቆጥር ስለምናገኛቸው አያቶቿ በስፋት ይነገራል፡፡ ቴክታና ጴጥርቃ ሳይወልዱ ብዙ ቆይተው በሕልም ቴክታ እንቦሳ ስትወልድ፣ እንቦሳይቱ ሌላ እንቦሳ ስትወልድ፣ እንዲህ እያሉ እስከ 6 ድረስ ይሔዱና ስድስተኛይቱ ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ያያሉ፡፡ ሕልም ፈቺም መልካም ሴት እንደሚወልዱ፣ እርሷም ሌላ መልካም ሴት እንደምትወልድ፣ እንደዚሁ እስከ ስድስተኛዋ ደርሰው ከፍጥረታት ሁሉ የምትበልጥ እንደምትወለድ ነግሯቸው የፀሐይ   ነገርን ግን አልተገለፀልኝም ይላቸዋል፡፡ ቴክታ ዴርዴን፣ ዴርዴ ሲካርን ፣ ሲካር ቶናን፣ ቶና ሔርሜላን፣ ሔርሜላ ሐናን ይወልዱና ጨረቃ የተባለችውን እመብርሃን ሐና ከኢያቄም ትወልዳለች፡፡ ጨረቃ የተባለችው እመቤታችንም ዘእንበለ ዘርአ ብእሲ (ካለ ወንድ ዘር) ፀሐይ የተባለውን እውነተኛውን ብርሃን ክርስቶስን ወለደችው፡፡ እመቤታችን አማናዊ ፀሓይ ክርስቶስን በመውለዷ ሊቃውንት አዲሲቷ ሰማይ ብለዋታል፡፡ ስለዚህ ድንግልን የብርሃን መገኛ፣ የብርሃን ደጅ - ኆኅተ ብርሃን እንላታለን፡፡

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ኆኅተ ብርሃን Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top