• በቅርብ የተጻፉ

    Friday 6 November 2015

    ታላቁ አባት ቅዱስ ዻውሊ

    በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

    =>አንድ ቀን ቅዱስ እንጦንስ (የመነኮሳት ሁሉ አባት) እንዲህ ሲል አሰበ:: "በውኑ በበርሃ ለበርካታ ዘመናት በመኖር ከእኔ የሚቀድም (የሚበልጥ) ሰው ይኖር ይሆን?"
    ይህንን ሃሳቡን ገና ሳይጨርሰው ቅዱስ ሚካኤል ወደ እርሱ ዘንድ ደረሰ::
    +"እንጦንስ ሆይ! ከእኔ የሚቀድም የበርሃ ሰው ይኖር ይሆን ብለህ አስበሃል::
    *በእርግጥም ከአንተ 20 ዓመታትን ቀድሞ ወደ በርሃ የገባ
    *በቅድስናው ፈጣሪውን ያስደሰተ
    *ዓለም ከነ ክብሯ የእግሩን መረገጫ ያህል እንኩዋ የማትመጥነው
    *በጸሎቱና በምልጇው ዓለም የምትጠበቅለት
    *ሞገስን የተሞላ አንድ ሰው በበርሃ ስላለ ሒድና ተመልከተው" ብሎት ተሠወረው::
    +ቅዱስ እንጦንስም ከሰማው ነገር የተነሳ እየተደነቀ ተነሳ:: እርሱ ካለበት በርሃ በራቀ መንገድም ለቀናት ተጉዞ አንድ በዓት (ዋሻ) በር ላይ ደረሰ:: በበሩ አካባቢ የሰውና የአራዊት ኮቴ ተመልክቶ በሩን ጸፋ (ቆፈቆፈ)::
    *በውስጥ ያለው አረጋዊ ሰው ግን ትልቅ ድንጋይ ገልብጦ በሩን አጠበቀው:: ለ80 ዓመታት ሰውን አይቶ አያውቅምና ሰይጣን ሊያታልለኝ መጥቷል ብሎ አስቧል:: ቅዱስ እንጦንስ ግን "ኃሠሥኩ እርከብ: ጐድጐድኩ ይትረኃው ሊተ (ማለትም ሽቻለሁና ላግኝ: ደጅ መትቻለሁና ይከፈትልኝ)" ሲል አሰምቶ ተናገረ::
    +ቅዱሱ ገዳማዊም ሰው መሆኑን ሲያውቅ በሩን ከፈተለትና ወደ ዋሻው አስገባው:: መንፈሳዊ ሰላምታንም ተለዋወጡ:: ሲመሽም ቅዱስ እንጦንስ ሽማግሌውን ገዳማዊ "ስምህ ማን ነው?" ቢለው "ስሜን ካላወክ ለምን መጣህ?" ሲል መለሰለት::
    +ያን ጊዜ ቅዱስ እንጦንስ ቀና ብሎ ሰማይን ሲመለከት ምሥጢር ተገለጠለትና "ቅዱስ ዻውሊ ሆይ! ከአንተ ጋር ያገናኘኝ ፈጣሪ ይክበር: ይመስገን" ሲል ፈጣሪውን ባረከ:: ቅዱስ ዻውሊም መልሶ (በጸጋ አውቆት) "አባ እንጦንስ ሆይ! እንኩዋን ደህና መጣህ" አለው:: 2ቱም ደስ ብሏቸው ፈጣሪያቸውን እያመሰገኑ ተጨዋወቱ::
    +" ቅዱስ ዻውሊ ማን ነው? "+
    =>ቤተ ክርስቲያን ለሁሉም ዓይነት የቅድስና ሕይወት የመጀመሪያ የምትላቸው አላት:: ለምሳሌ:-
    *የመጀመሪያው ሐዋርያ ቅዱስ እንድርያስ
    *የመጀመሪያው ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ
    *የመጀመሪያው መነኮስ ቅዱስ እንጦንስን እና
    *የመጀመሪያውን ባሕታዊ (ገዳማዊ) ቅዱስ ዻውሊን ማንሳት እንችላለን::
    +ቅዱስ ዻውሊ የተወለደው በሰሜናዊ ግብጽ: በእስክንድርያ ከተማ ሲሆን ዘመኑም 3ኛው መቶ ክ/ዘመን መጀመሪያ ላይ ነው:: ወላጆቹ ባለጸጐች ነበሩ:: ቅዱሱንና ታላቅ ወንድሙን አባ ዼጥሮስን ወልደዋል:: 2ቱ ክርስቲያን ወንድማማቾች ገና ወጣት ሳሉ ወላጆቻቸው ሞቱባቸው:: ሃዘናቸውን ፈጽመው ሃብት ሲካፈሉ ግን መስማማት አልቻሉም::
    +ምክንያቱ ደግሞ ትልቁ ዼጥሮስ ደህና ደህናውን እቃ ወስዶ መናኛ መናኛውን ለትንሹ ለዻውሎስ (ዻውሊ) መስጠቱ ነበር:: ስለዚህ ነገር ተካሰው ወደ ፍርድ ቤት ሲሔዱ ግን መንገድ ላይ አንድ ባለጸጋ ሙቶ ደረሱ::
    +ቆመው ሳሉም ቅዱስ መልአክ ሰው መስሎ ዻውሊን "ይህ ሰው ባለጸጋ ነው:: በገንዘቡ የሰጠውን ፈጣሪ ሲበድልበት ኑሮ እነሆ ተሸኘ:: በሰማይም አስጨናቂ ፍርድ ይጠብቀዋል" ሲል ነገረው::
    +በዚያች ቅጽበት የወጣቱ ዻውሊ ሐሳብ ተለወጠ:: ወደ ወንድሙ ተመልሶ "ወንድሜ ሆይ! ሁሉ ንብረት ያንተ ይሁን" ብሎት ከአካባቢው ጠፋ:: በመቃብር ሥፍራ ለ3 ቀናት ያለ ምግብ ጸልዮ የእግዚአብሔር መልአክ ሰው ወደ ማይደርስበት በርሃ ወሰደው::
    +በዚያም ምንጭ ፈለቀችለት:: እየጾመ ይጸልይ: ይሰግድ ገባ:: ሁሌ ማታ ግማሽ ሕብስት ከሰማይ እየወረደለት: ቅዳሜና እሑድ መላእክት እያቆረቡት ለ80 ዓመታት ኖረ:: (አንዳንድ ምንጮች ግን ለ90 ዓመታት ይላሉ) ከቅዱስ እንጦንስ ጋር የተገናኙትም ከዚህ በሁዋላ ነው::
    +ከቅዱስ እንጦንስ ጋር በነበራቸው የ2 ቀናት ቆይታም ቅዱስ ዻውሊ ብዙ ትንቢቶችን ተናግሯል:: በዚህች ቀን ሲያርፍም መቃብሩን አናብስቱ ቆፍረዋል::
    +ቅዱስ እንጦንስም በክብር ቀብሮታል:: 80 ዓመት የለበሳት የዘንባባ ልብሱም ሙት አስነስታለች::
    << ጻድቅ: ቡሩክ: ቀዳሚው ገዳማዊ: መላእትን የመሰለና የባሕታውያን ሁሉ አባት ለተባለ ለቅዱስ ዻውሊ ክብር ይገባል >>
    +"+ ገዳማዊ ሕይወት +"+
    =>በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ "ታላቁ / ዓቢይ / THE GREAT" የሚል ስም የሚሰጣቸው አባቶች የተለዩ ናቸው:: አንድም እጅግ ብዙ ትሩፋቶችን የሠሩ ናቸው:: በሌላ በኩል ደግሞ በተመሳሳይ ስም ከሚጠሩ ሌሎች ቅዱሳን እንለይበታለን::
    +ገዳማዊ ሕይወት ጥንቱ ብሉይ ኪዳን ነው:: በቀዳሚነትም በደብር ቅዱስ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ደቂቀ ሴት እንደ ጀመሩት ይታመናል:: ሕይወቱ በጐላ: በተረዳ መንገድ የታየው ግን በታላቁ ጻድቅ ሄኖክ: ከዚያም በቅዱሱ ካህን መልከ ጼዴቅ አማካኝነት ነው::
    +ቀጥሎም እነ ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ: እነ ኤልሳዕ ደቀ መዝሙሩ ኑረውበታል:: በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ሙሉ ሕይወቱን በገዳም (በበርሃ) ያሳለፈው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቅድሚያውን ይይዛል::
    +ለስም አጠራሩ ስግደት ይሁንና መድኃኒታችን ክርስቶስ በገዳመ ቆረንቶስ ለ40 ቀናት በትሕርምት ኑሮ ገዳማዊ ሕይወትን ቀድሷል: አስተምሯል:: በዘመነ ስብከቱም ያድርባት የነበረችው የደብረ ዘይቷ በዓቱ (ኤሌዎን ዋሻ) በራሷ ለዚህ ሕይወት ትልቅ ማሳያ ናት::
    +ከጌታ ዕርገት በሁዋላም ክርስቲያኖቹ የዓለም ሁካታ ሲሰለቻቸው: አንድም በንጹሕና በተሸከፈ ልቡና ለፈጣሪያቸው መገዛትን ሲሹ ከከተማ ወጣ እያሉ ይኖሩ እንደ ነበር የታሪክ መዛግብት ያሳያሉ:: አኗኗራቸውም በቡድንም: በነጠላም ሊሆን ይችላል::
    +ዋናው ነገር ግን በጾምና በጸሎት መትጋታቸው ነው:: ይሕም ሲያያዝ እስከ 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ደረሰ:: በዚህ ዘመን ግን አባ ዻውሊ የሚባል ንጹሕ ክርስቲያን ይሕንን ሕይወት ወደ ሌላ ደረጃ ከፍ አደረገው:: ለ80 ዓመታት ሰው ሳያይ ተጋድሎ 'የባሕታውያን አባት' ተባለ:: ደንብ ያለው ተባሕትዎም ጀመረ::
    +ይህ ከሆነ ከ20 ዓመታት በሁዋላ ደግሞ አባ እንጦንስ የሚባሉ ደግ ክርስቲያን ይህንን ገዳማዊ ሕይወት በሌላ መንገድ አጣፈጡት:: በቅዱስ ሚካኤል አመንኩዋሽነት ገዳማዊ ሕይወት በምንኩስና ተቃኘ:: ስለዚህም አባ እንጦንስ የመነኮሳት አባት ተባሉ::
    +እርሳቸውም ሕይወቱን ለማስፋፋት ከተለያዩ አሕጉር ደቀ መዛሙርትን እየተቀበሉ አመንኩሰዋል:: ቅዱሳን የአባ እንጦንስ ልጆችም ወደየ ሃገራቸው ተመልሰው: ሕይወቱን በተግባር አሳይተው ገዳማዊነትን አስፋፍተዋል::
    =>አምላክ በበረከታቸው ይባርከን::
    =>የካቲት 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
    1.ቅዱስ አባ ዻውሊ ገዳማዊ (የባሕታውያን ኁሉ አባት)
    2.ቅዱስ አባ ለንጊኖስ ሊቀ ምኔት (ደብረ ዝጋግ-ግብፅ)
    3.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
    =>ወርሐዊ በዓላት
    1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
    2.ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ
    3.ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ (የሃይማኖት ጠበቃ)
    4.ቅዱስ ኢዮብ ጻድቅ
    5.ቅዱስ አቤል ጻድቅ
    6.አባ ሕርያቆስ ዘሐገረ ብሕንሳ
    =>+"+ የሚበልጠውን ትንሳኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ:: ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ:: በድንጋይ ተወግረው ሞቱ:: ተፈተኑ: በመጋዝ ተሰነጠቁ: በሰይፍ ተገድለው ሞቱ:: ሁሉን እያጡ: መከራን እየተቀበሉ: እየተጨነቁ: የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ:: ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ: በዋሻና በምድር ጉድጉዋድ ተቅበዘበዙ:: +"+ (ዕብ. 11:35-38)
    <ወስብሐት ለእግዚአብሔር>

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ታላቁ አባት ቅዱስ ዻውሊ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top