• በቅርብ የተጻፉ

    Friday 13 November 2015

    አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ (2ቆሮ 5-14)


    ከጌታችንና ከአምላካችን ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊት መሰቀል የወንበዴ መቅጫ መሳሪያ ነበር። ሰውን በመስቀል ላይ መቅጣት የተጀመረው በፋርስ ነው። ፋርስ የዛሬዋ ኢራን ናት።የፋርስ ሰዎች “ኦርሙዝድ” የተባለ “የመሬት አምላክ” ያመልኩ ነበር። ከዚህም የተነሳ ”ወንጀለኛው ቅጣቱን በመሬት ላይ የተቀበለ እንደሆነ አምላካችን ይረክሳል” ብለው ስለሚያምኑ ወንጀለኛውን ከመሬት ከፍ አድርገው በመስቀል ላይ ይቀጡት ነበር። ይህም ቅጣት ቀስ በቀስ በሮም ግዛት ሁሉ የተለመደ ህግ ሆነ። ከዚህም ሌላ በኦሪቱ ስርዓት ቅጣታቸውን በመስቀል ላይ የሚሰቀሉ ሰዎች ርጉማንና ውጉዛን ነበሩ። ይህንንም እግዚአብሄር ለሙሴ “ማንም ሰው ለሞት የሚያበቃውን ሃጥአት ቢሰራ፤ እንዲሞትም ቢፈረድበት፤ በእንጨትም ላይ ብትሰቀለው በእንጨትም ላይ የተሰቀለ በእግዚአብሔር ዘንድ የተረገመ ነውና ሬሳው በእንጨት ላይ አይደር” ሲል ነግሮታል(ዘዳ.21፦22)።

    ትምህርት

    “በመስቀል ላይ ተሰቅሎ የሚሞት የተረገመ ከሆነ ለምን ጌታችን በመስቀል ተሰቅሎ ሞተ?”

    ·         ቅጣታችንን ተቀብሎ ሞተ፦የሁላችንንም በደል በራሱ ላይ አኖረ።(ኢሳ.53፦6)

    ·         የእኛን ሞት ሞተ፦በአንድ ሰው ምክንያት ሞት ወደዓለም ገባ ተብሎ አንደተጻፈው (ሮሜ.5፦15)

    ·         ፈውስ እናገኝ ዘንድ ሞተ፦በእርሱ ቁስል አኛ ተፈወስን።(ኢሳ53፦5)

    ·         ገነትን አንወርስ ዘንድ መርገማችንን ወስዶ ሞተ፦በእንጨት የተሰቀለ የተረገመ ነው። ተብሎ እንደተጻፈው(ዘዳ.21፦23)

    ·         ሙታንን ያነሳ ዘንድ ሞተ

    ·         የዳያብሎስን ምክር ያፈርስ ዘንድ ሞተ


    አንዱ ስለ ሁላችን ሞቶ ምን አገኘን?

    1.  ሕወትን አግኝተናል፤

    በኃጥያት ምክንያት ሞት ገዝቶን ሞት ነግሶብን እነኖር ነበር። ኃጢአት በዘር የእተላለፈም ሁላችንም በአዳም ኃጢአት ምክንያት እንሞት ነበር።በመሆኑም ሞት ከአዳም እስከ ሙሴ ድረስ በሰው ልጆች ሁሉ ላይ ነግሶ ነበር(ሮሜ5፦12)። ከክርስቶስ ሞት በኋላ ግን በክርስቶስ ሞት ስለተሻረ አጥተነው የነበረውን ሕይወት አግኝተናል።”ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና” (1ኛቆሮ፣15፦22)። በተጨማሪም “እኛ ሁላችን ደግሞ በስጋ ምኞት እንኖር ነበር፤ አንደሌሎቹም ደግሞ ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን።  ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለጠጋ ስለሆነ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሳ በበደላችን ሞታን እንኳ በሆንን ጊዜ ሕይወትን ሰጠን (ኤፌ.2፦3-5)።

    ኃጢአት ወደ ዓልም ገብቶ ሞት የመጣብን በመብል ምክንያት ነው።(ዘፍ.3፦1-24)

    2.  ሰላምን አግኝተና፤

    ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፦”ሰላምን እተውላችኋለሁ ሰላሜን አሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ሰላም ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም፤” ብሎ እንደተናገረ ፍጹም የሆነውን ሰላም የሰጠን በመስቀል ላይ ነው።

    3.  አዲስ ሰው ሆነናል፤

    በኃጢያት አርጅቶ የነበረው ሰውነታችን አዲስ የሆነው በመስቀል ላይ በተፈጸመው ቤዛነት ነው። “ከአንግዲህስ ወዲያ በኃጢአት አንዳንገዛ የኃጢአት ስጋ ይሻር ዘንድ አሮጌው ሰውነታችን ከእርሱ ጋር አንደተሰቀለ እናውቃለን።(ሮሜ.6፦6)

    4.  ከራሱ ጋር አስታረቆናል፤

    በኃጢያት ምክንያት ከእግዚአብሔር ጋር ተጣልተን አንኖር ነበር።ይሁን አንጂ አኛ በበደልን አርሱ ክሶ በቤዛነቱ መልሶ ታርቆናል።”ጠላቶቹ ሳለን ከእግዚያብሔር ጋር በልጁ ሞት ከተታረቅን፦ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ አንድናለን፤ ይህም ብቻ አይደለም፦ነገር ግን አሁን መታረቁን ባገኘንበት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በእግዚአብሔር ደግም አንመካለን፤”(ሮሜ.5፦10)።

    መልእክት

    አንዱ ስለ ሁላችን ሞተ፣ የእኛን ቅጣት ወሰደ፣ እኛ በእርሱ ሞት ወደ ቀደመ ክብራችን እንመለስ ዘንድ ሞተ ።መርገማችንንም ወሰደ።የኢየሱስ ክርስቶስን ስቅለት ስናስብ የተጣላን መታረቅ አለብን። የኢየሱስ ክርስተቶስ ሞት የሰው ልጆች የጥል ግድግዳ ፈርሶ ፍቅር የተመሰረተበት ዕለት ነውና።ይህን ውለታ አንዳንረሳ።

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ (2ቆሮ 5-14) Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top