• በቅርብ የተጻፉ

    Saturday 14 November 2015

    ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ


    ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

    ቅድስት አርሴማ እናታችን ከአባቷ ከቅዱስ ቴዎድሮስና ከእናቷ ቅድስት አትናሲያ በስዕለት ተወለደች፡፡ ቤተሰቦቿ እግዚአብሔርን በቅንነት ያገለግሉ ከነበሩ ከከበሩ ካህናት ወገን እንደነበሩ የገድሏ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡

    ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ ቅዱሳት መጻሕፍትን ከቤተሰቦቿ በሚገባ የተማረች፤ የተማረችውንም በተግባር የተረጎመች፤ በጸሎት ሕይወት የምትተጋ ከቅዱሳት አንስት አንዷ ናት፡፡ ይቺ ታላቅ ሰማዕት በነበረችበት ዘመን በአርመን የነገሠው አረማዊ ንጉሥ ድርጣድስ ይባላል፡፡ ይህ ንጉሥ እግዚአብሔር አምላክ በሙሴ ላይ አድሮ “ቀልጠው የተሠሩትን የአማልክት ምስሎች ለአንተ አታድርግ”ብሎ የተናገረውን በመቃወም ለጣዖት የሚሰግድ ፀሐይንም ያመልክ ነበር /ዘጸ.34፥17/፡፡ በዘመኑ የነበሩ ክርስቲያኖችን “እኔ ለማመልከው “አምላክ” ወይም ጣዖት መስገድ አለባችሁ፤ ይህን የማታደርጉ ከሆነ ትእዛዜን ጥሳችኋልና መከራ ይጸናባችኋል” የሚል ዐዋጅ በማውጣት መከራ ያደርስባቸዋል፡፡
    ጨካኙ ንጉሥ ድርጣድስ ይህን ትእዛዙን ባለማክበራቸው መከራና ስቃይ ያደረሰባቸው ክርስቲያኖች ቁጥራቸው 27 ናቸው፡፡ “እኔን የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሌንም ተሸክሞ ይከተለኝ”ያለውን የእግዚአብሔርን ሕግ የፈጸሙ ክርስቲያኖች እሱ ለሚያመልከው ለጣዖት አንሰግድም በማለታቸው ይደበድባቸውና ግፍና መከራ ያጸናባቸው ጀመር፡፡ ይህን ግፍና መከራ የተመለከተች እናታችን ቅድስት አርሴማ የተጋድሎ ሕይወትን እነሱን አብነት አድርጋ እንደ ጀመረች የሕይወት ታሪኳን የያዘው መጽሐፏ ይነግረናል፡፡

    ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ‘‘ነገር ግን ወደ ሸንጎ አሳልፈው ይሳጧችኋል፤ በምኩራቦቻቸውም ይገርፏችኋልና ከሰዎች ተጠበቁ! ለእነርሱና ለአሕዛብም ምስክር እንዲሆን ስለ እኔ ወደ ገዢዎች ወደ ነገሥታትም ትወሰዳላችሁ… አትጨነቁ! በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ የምትናገሩት እናንተ አይደላችሁም” /ማቴ.10፥16-20/፡፡ ብሎ የተናገረውን በማሰብ ቅድስት አርሴማ በሃያ ዓመቷ የንጉሡን እኩይ ግብሩን በመንቀፍ ስለ ክርስቶስ ከሚሰቃዩ ሰማዕታት ወገኖቿ ጋር በመሆን ስለ እግዚአብሔር አምላክነት ትመሰክር ነበር፡፡
    የንጉሡም አገልጋይ በደም ግባቷና በንግግሯ ማማር ተደንቆ በዚች በፈቃዷ ሰማዕትነትን ልትቀበል በወደደች ሴት ምንም ሊያደርግባት ስላልወደደ ወደ ንጉሡ ወደ ድርጣድስ ከሃያ ሰባቱ ክርስቲያኖች ጋር ወሰዳት፡፡ ንጉሡም ብዙ የተነገረላትን ወጣት ሲያይ በውበቷና በንግግሯ ተማርኮ ለዓለማዊ ደስታውና ፍላጎቱ ተመኛት፡፡ ሚስት ትሆነው ዘንድ አብዝቶ ተማጸናት፡፡ እጅ መንሻና ማታለየ የዚህን ዓለም ወርቅና ብር አቀረበላት፡፡ ቅድስት አርሴማ ግን መልክ ረጋፊ፤ የዚህ ዓለም ሀብትም ከንቱ እንደሆነ ስለምታውቅ በዓላማዋ ጸናች! ንጉሡንም ‘‘እኔ የንጉሥ የክርስቶስ ሙሽራ እንጂ የዚህን ዓለም አላፊ ጠፊ የሆነውን ገንዘብና ደስታ የምሻ አይደለሁም፡፡’’በማለት መለሰችለት፡፡

    ንጉሡም ይህንን ከእርሷ በመስማቱ እጅግ ተቆጣ፤ እግዚአብሔር አምላኳን በማመኗ ተበሳጨ፤ አሽከሮቹንም ጠርቶ በቤተ መንግሥቱ የታሠሩትን አንበሶች እንዲለቀቅባቸው አዘዘ፡፡ አንበሶቹ ግን ይደሰቱ ነበር፡፡ በኋላም ፊታቸውን ወደ ንጉሡና አገልጋዮቹ በማዞር ሩጠው እስኪደበቁ ድረስ አሳደዷቸው፡፡
    በቅድስት አርሴማ የገድል መጽሐፍ ላይ የሰፈረው ታሪክ በተመሳሳይ መልኩ በትንቢተ ዳንኤል ላይ ሲፈጸም እናያለን፡፡ ነቢዩ ዳንኤል ያለ በደሉ በክፉ ሰዎች ምክር የተራቡ አንበሶች ወዳሉበት ጉድጓድ በተጣለ ጊዜ አንበሶቹ ፈጽሞ ጉዳት አላደረሱበትም፣ እንኳን ሊበሉት የእግሩን ጥፍር እየላሱ ተገዝተውለታል፡፡ “በነጋውም ንጉሡ ማልዶ ተነሣ ፈጥኖም ወደ አንበሶቹ ጉድጓድም ወደ ዳንኤል በቀረበ ጊዜ በኃዘን ቃል ጠራው፤ ንጉሡም ተናገረ ዳንኤልንም፡- የሕያው አምላክ ባሪያ ዳንኤል ሆይ ሁልጊዜ የምታመልከው አምላክህ ከአንበሶች ያድንህ ዘንድ ችሎአልን? አለው፡፡ ዳንኤልም ንጉሡን ንጉሥ ሆይ ሺህ ዓመት ንገሥ በፊቱ ቅንነት ተገኝቶብኛልና በአንተም ፊት ደግሞ ንጉሥ ሆይ አልበደልሁምና አምላኬ መልአኩን ልኮ የአንበሶችን አፍ ዘጋ፤ እነርሱም አልጎዱኝም አለው” የዳንኤል ከሳሾች ግን “በአንበሶች ጉድጓድ ጣሏቸው፤ ወደ ጉድጓዱም መጨረሻ ሳይደርሱ አንበሶች ያዟቸው ዐጥንታቸውንም ሁሉ ሰባበሩ” /ዳን. 6፥19-25/፡፡
    ንጉሡ የክርስቲያኖቹ በሰማዕትነት መጽናት ስለነደደው በረሃብ እንዲያልቁ እንዲታሠሩ አዘዘ፡፡ እግዚአብሔርም በአምስተኛው ቀን በብርሃን ቤቱን ሞልቶት የሚበሉትን በመሶብ የሚጠጡትን በጽዋ ከሰማይ አወረደላቸው፡፡

    ንጉሡም ይህንን በማየቱ ከዚያ አውጥቶ በእሳት ውስጥም አስገባቸው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ ከእሳት ያወጣቸው እግዚአብሔር አምላክ እነርሱንም አዳናቸው፡፡ የክርስቲያኖቹ የእምነት ጽናት የሚደንቅ ስለነበር ንጉሡ አማካሪዎቹ ጠርቶ “ምን ብናደርግ ይሻላል?” የሚል ምክር ጠይቆ ሁሉንም በሰይፍ ተሰይፈው እንዲሞቱ ስምምነት ላይ ይደርሳል፡፡
    እያንዳንዳቸውን ተራ በተራ ሲሰይፋቸው ቅድስት አርሴማ ለሚሰየፉት ሁሉ የድል አክሊል ከሰማይ ሲወርድላቸው ትመለከት ስለነበር የእርሷን ተራ በጉጉት ትጠብቀው ነበር፡፡ በሰማዕትነት አምላኳ እንዲያጸናት እየጸለየች “አይዟችሁ ጽኑ! የዚህ ዓለም መከራ አያሰቅቃችሁ! አትፍሩ” እያለች ታጽናናቸው ነበር፡፡
    ንጉሡም ሌሎቹን አሰይፎ ሲያበቃ ወደሷ ዞሮ በቁጣ እየጮኸ “አንቺን እንደ ባልንጀሮችሽ በቀላሉ አልገልሽም! ስቃይ አጸናብሻለሁ” ብሎ ለአገልጋዮቹ ትእዛዝ በመስጠት ዓይኗን አስወጥቶ በእጇ እንድትይዝ አደረጋት፤ ጡቷን ቆረጣል፤ በኋላም አንገቷን በሰይፍ በመቅላት መስከረም 29 ቀን በሰማዕትነት እንድታልፍ አድረጋት፡፡
    ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ‘‘ከመረጥኳቸው ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ’’እንዲል /መዝ. 8፥3/፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‘‘በእኔ ስም አምነሽ የዚህ ዓለም ተድላና ደስታ ሳያታልልሽ አንገትሽን ለሰይፍ ሰጥተሽ ተሰይፈሻል፤ የሰማዕትነት ተጋድሎ ፈጽመሻልና ስምሽን የጠራ፤ በዓልሽን ያከበረ፤ ዝክርሽን ያዘከረ፤ ገድልሽን የጻፈና ያጻፈ፤ የሰማና ያሰማም እስከ 12 ትውልድ ድረስ እምርልሻለሁ’’ ሲል ቃል ኪዳን ገብቶላታል፡፡
    የተወደዳችሁ የዓምደ ተዋሕዶ ጦማር አንባብያን የሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ ዓመታዊ ክብረ በዓል መታሰቢያ ምክንያቱ ይህ እንደሆነ በማሳሰብ፤

    የቅድስት ባርባራ ሥዕል የእሷ እየመሰል የምንጠቀም ብዙዎች ነንና ለይተን እንድንጠቀም የመጨረሻ መልእክታችን ነው፡፡
    የሰማዕቷ የቅድስት አርሴማ ረድኤት በረከት ጸሎትና ምልጃ ከሁላችን ጋር ይኑር፡፡ አሜን! !

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top