• በቅርብ የተጻፉ

    Tuesday 24 November 2015

    ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኡል ፡ ታህሳስ 19


         ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱና በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ታማኝ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ በተረዳኢነቱና በአማላጅነቱ በክርስቲያኖች ዘንድ ይወደዳል፡፡ምክንያቱም ያዘኑትን ለማፅናናት የምስራች ለመንገር ከእግዚአብሔር ወደ ምእመናን ያላካልና፡፡

          ገብርኤል ማለት የእግዚአብሔርን ልጅ የሚመስል ጌታና አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱሳን ሰማዕታት ገድላቸውን እንዲፈፅሙ እሳቱንና ስለቱን ተሳቀው ወደ ኋላ እንዳይመለሱ ይረዳቸዋል፡፡ 

         ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያናችን የቅዱሳን መላዕክትን ወርሃዊና ዓመታዊ በዓላቸውን በፀሎትና በምስጋና ታከብራለች፤ በተለይ ታህሳስ 19 ቀን የሚከበርበት ምክንያት ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሠለስቱ ደቂቅን ከዕቶን እሳት ያዳነበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡

       በጣዖት ፍቅር እጅግ ያለመጠን ልቡ ተቃጥሎ የነበረው የባቢሎን መሪ ነቡከደነፆር ቁመቱ ስድሳ ወርዱ ስድስት ክንድ የሆነውን የወርቅ ምስል አሰርቶ መኳንንቱን ሰብስቦ ሕዝቡ በሙሉ ለጣዖቱ እንዲሰግድ አዋጅ አወጀ፡፡ ያ ዘመን ለእግዚአብሔር ወዳጆች የፈተና ዘመን ነበር፡፡ አስመሳዮች ለጣዖት ሰገዱ፤ ተረበረቡ፡፡ እውነተኛ አማኞች ግን በእግዚአብሔር ላይ ያላቸውን እምነት ‹‹ ንጉስ የወደደው፣ ጊዜ የወለደው›› በሚል አስተሳስብ አይለወጥም፡፡ በዚያ ፈታኝ ዘመን ነበር ሶስት ታማኝ የእግዚአብሔር ባለሟሎች የተገኙት፡፡ 
    ንጉሱ ላቆመው ጣኦት ያልሰገደ ወደ እቶን እሳት ተጥሎ እንደሚሞት ቁርጥ ውሳኔው መሆኑን ወጣቶቹ በሚገባ ያውቁታል ግን ይህንን አልፈሩም፡፡ ንጉስ ሆይ አምላካችንን ክደን አንተ ላቆምከው ጣዖት አንሰግድም አሉት፡፡ ሶስቱ ወጣቶች የወሰዱት ይህ አቋም ለንጉሱ ታላቅ ራስ ምታትን  ፈጠረ፤ ንጉሱም አገልጋዮቹን ጠርቶ እሳቱ ሰባት እጥፍ እንዲነድ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡

    እሳቱም ሰባት እጥፍ ነደደ፡፡ ወዲያውኑ የንጉሱ አገልጋዮች አናንያ ፣ አዛርያን እና ሚሳኤልን እያንከበከቡ ወደ ዕቶን እሳቱ ወረወሯቸው፡፡ በእሳቱ ሀይል የተነሳ አገልጋዮቹም በእሳቱ እየተጠለፉ እንደ ማገዶ ነደዱ፡፡ ሠልስቱ ደቂቅ ግን ከየት እንደመጣ ከማይታወቅ  እንግዳ ጋር በመሆን በዕቶን እሳት ውስት ይንሸራሸሩ ጀመር፡፡ ይህ ተዓማራት ንጉሱንና መኳንንቱን አስገረመ፡፡  ንጉሱም በዚህ ወቅት 
            ‹‹ እነሆ እኔ በእሳቱ መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎች አያለሁ እሳቱ ምንም አላቆሰላቸውም አራተኛውም የአማልክትን ልጅ ይመስላል ፡፡ ››  አለ፡፡
        ንጉስ ናብከደነፆር በግልፅ ተመልክቶ እንደመሰከረው የነደደውን እሳት በማብረድ ለሠልስቱ ደቂቅ ቤዛ የሆናቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡  በግዕዙ ‹‹ ወገፁ ለራብዓይ ወልደ እግዚአብኤር ይመስል›› አራተኛውም ፊቱ የእግዚአብሔርን ልጅ ይመስላል ይላል፡፡


         አዎን፤ ከዚህ በላይ እንደተገለፀው ሊቀመላዕክት ቅዱስ ገብርኤል ስለ ሀይማኖታቸው መከራ የተቀበሉትን ወጣቶች የነደደውን እሳት አብርዶ በሃይማኖታቸው እንደአፀናቸው ተመልክተናል፡፡ 
    የቅዱስ ገብርኤል አማላጅነት እኮ ጥንት የነበረ ብቻ ሳይሆን እስከ አለንብት ዘመን ደርሶ የመልአኩን አማላጅነት በዓይን የተመለከትነው ተጨባጭ ድርጊት ነው፡፡

         የነደደ እሳት ውስጥ ገብቶ ከመውጣት ባልተናነሰ መከራ ውስጥ ገብተው በቅዱስ ገብርኤል አማላጅነት ከሞተ ስጋ ነፍስ ድነው እውነተኛ  ምስክርነታቸውን የሚሰጡ ብዙዎች ናቸው፡፡ በመልዓኩ ስም በፈለቀው ፀበል ተጠምቀው ደዌ የራቀላቸው እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ በየዓመቱ በቁልቢና በቅዱስ ገብርኤል ስም በታነፁአብያተ ክርስቲያናት የሚሰባሰበው ምዕመን ስዕለቱ የሰመረለት ልመናው የተሰማለት እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ስለዚህ ለመላዕክት አለቃ ለቅዱስ ገብርኤል የተሰጠውን ፀጋ ተረድተን መልአኩን ልናከብረውና ልናመሰግነው ይገባል፡፡

    መለከት ፡ ታህሳስ 1986 ዓ.ም

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኡል ፡ ታህሳስ 19 Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top