• በቅርብ የተጻፉ

    Saturday 14 November 2015

    ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ


    ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ: በገሊላ አካባቢ አድጐ: ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል:: ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር:: ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕጻን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው:: ይህ አባት መስከረም አራት ቀን በዚች ዕለት እንደተወለደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡

    ዮሐንስ የሚለው ስም ዮሐናን ከሚለው ቃል የተገኘ ሲኾንትርጓሜውም “ከያሕዌ (ከእግዚአብሔር) የተሰጠ” ማለትእንደኾነ ብዙ ሊቃውንት ይስማማሉ፡፡ ትርጓሜ ወንጌል ግን“ዮሐንስ ማለት ፍስሐ ወሐሴት ማለት ነው” ይላል፡፡ ቅዱስዮሐንስ ብዙ ቅጽል ስሞች አሉት፡፡ ከእነዚኽም መካከል፡-

    የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት በመግለጡናለጌታችን ባለው ቅንዓት ባሳየውም የኃይል ሥራ “ቦኤኔርጌስ-ወልደ ነጐድጓድ” /ማር.፫፡፲፯/፣የእግዚአብሔርን አንድነትና ሦስትነት ስለሚናገር “ታዖሎጐስ-ነባቤ መለኰት”፣ኃላፍያትንና መጻእያትን ስለሚናገር “አቡቀለምሲስ-ረአየኅቡአት- ባለ ራዕይ”፣እንዲሁም የጌታን ጸዋትወ መከራ አይቶ ፊቱ በኃዘን ተቋጥሮይኖር ስለ ነበር “ቁጹረ ገጽ- ፊቱ በሐዘን የተቋጠረ” ይባላል፡፡ጌታችን ግርማ-መንግሥቱን ሲገልጥ /ማቴ.፲፯፡፩/፣ የኢያኢሮስንልጅ ሲያነሣ /ማር.፭፡፴፯/፣ በጌቴሴማኒ የአታክልት ቦታ ሲጸልይ/ማቴ.፳፮፡፴፯/፣ ስለ ኢየሩሳሌም መጥፋት ትንቢት ሲናገር/ማር.13፡3/ ዮሐንስ አብሮ ስለ ነበር “የምሥጢር ልጅ”ምይባላል፡፡ቅዱስ ጳውሎስ አዕማደ ቤተ ክርስቲያን ብሎ ከሚጠራቸው ሐዋርያት አንዱ ዮሐንስ ነው /ገላ.፪፡፱/፡፡ከሌሎቹ ደቀ መዛሙርት በተለየ አኳኋንም ጌታን ይወደው ስለነበር ሁሌ ከእቅፍ አይለይም ነበር፡፡ በዚህም “የጌታ ወዳጅ-ፍቁረ እግዚእ” ተብሏል /ዮሐ.፲፫፡፳፫/፡፡ከነዚህ በተጨማሪ ወንጌላዊው፣ ሐዋርያው፣ ድንግል፣ ዘንሥር፣ዘረፈቀ ውስተ ህፅኑ ለኢየሱስ፣ ካልእ ረድእ፣ ባሕረ ጥበባት፣አበ ልሳናት… እየተባለም ይጠራል፡፡

    የቅዱስ ዮሐንስ አባቱ ዘብዴዎስ የሚባል የሲዶና ሀገር ገሊላዊ ሲሆንዓሣ አጥማጅ ነበር፡፡ እናቱም ማርያም ባውፍልያ እንደምትባልናከ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት አንዷ መኾኗን የቤተ ክርስቲያናችንትውፊት ያስረዳል /ማቴ.፳፰፡፩/፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስ በመጀመርያ የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙር ነበር/ዮሐ.፩፡፴፭-፵/፡፡ በኋላ ግን ከታላቅ ወንድሙ ከያዕቆብ ጋር ሰዎችንእንደ ዓሣ በወንጌል መረብ ከዚሁ ዓለም ባሕር ለማጥመድ ጌታችንኢየሱስ ክርስቶስ የስብከት ሥራውን እንደ ጀመረ በቅፍርናሆምከተማ በገሊላ አጠገብ ሲመላለስ ሳለ ጠራው /ማቴ.፬፡፳፩/፡፡ እርሱምወዲያው ከወንድሙ ጋር ታንኳይቱንና አባቱን ትቶ ተከተለው፡፡ጌታችን ሲጠራው የ፳፭ ዓመት ወጣት እንደ ነበረም ሄሬኔዎስ የተባለደቀ መዝሙሩ ጽፏል፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱ ኹሉ የተለየ ፍቅር ስለነበረውጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ ተከትሎታል፡፡ ለዚኽምመላው የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖችን ወክሎ የእመቤታችንንእናትነት ከጌታ ተቀብሏል፡፡ በዚያች የመከራና የኑዛዜ ሰዓት የተገኘየቁርጥ ቀን ወዳጅ በመኾኑ በአደራ መልክ “እነኋት እናትኽ”ተብሏል፡፡ እርሱም ለእመቤታችን ልዩ አክብሮትና ፍቅር ስለነበረውበእናትነት ተቀብሎ ወደ ቤቱ ወስዷታል፡፡ አደራውን አክብሮበመጠበቅና በማጽናናትም ፲፮ ዓመት ሲታዘዛት ኖሯል /ዮሐ.፲፱፡፳፭-፳፯/፡፡

    ሐምሌ ፭ የሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር እንደሚገልጠው ቅዱስዮሐንስ የስብከቱን ሥራዉን በኢየሩሳሌምና በአከባቢው የጀመረውወደ አንጾክያ ሄዶም ያስተማረው ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር ነው፡፡ከኢየሩሳሌም እስከ አንጾክያ በፈረስ ፳ ቀን ያስኬዳል፡፡ ቅዱስዮሐንስና ቅዱስ ጴጥሮስ ግን በእግዚአብሔር ርዳታ በአንዲት ሌሊትደረሱ፡፡ ዮሐንስም ወደ ከተማይቱ ቀደም ብሎ ገባና ስለ ሀገሩ ጥናትሲያደርግ የሀገሩ ሰዎች እጅግ ክፉዎች እንደኾኑ ተረዳ፡፡ ምንምእንኳ በክፋታቸው ቢያዝንም ቅዱስ ጴጥሮስ አጽናንቶ አደፋፈረውናወደ ከተማይቱ ገብተው በክርስቶስ ስም ወንጌልን ሰበኩ፡፡ ጣዖትንከሚያመልኩ ሰዎች ብዙ መከራ ቢደርስባቸውም በአንጾክያ ውስጥተአምራትን እያደረጉና በስብከት በክርስቶስ ወንጌል ብዙ ሰዎችንአሳመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ ሌላ ያስተማረባት ሀገር ሎዶቅያእንደምትባል ስንክሳሩ ይገልጣል፡፡ በከተማ አጠገብ ያለ ቄድሮስየሚባል ወንዝ ሞልቶ የሀገሪቱን ብዙ ንብረት በወደመ ጊዜ ቅዱስዮሐንስ ከቅዱስ ጴጥሮስ ዘንድ ሄደና በተአምራት የውኃውን ሙላትአቆመላቸው፡፡ ወደ ከተማዋም ገብቶ ብዙ ተአምራትን እያደረገወንጌልን ሰበከ፡፡ ካዩት ተአምራትና ከሰሙት ትምህርት የተነሣምብዙዎች አመኑ፡፡

    ጥር ፬ በሚነበበው ስንክሳር እንደምናነበው ደግሞ ቅዱስ ዮሐንስ በሕይወቱ መጨረሻ አከባቢ ያስተማረው በእስያ ሀገር ሲኾን ዋናመንበሩም ኤፌሶን ነበረች፡፡ ዮሐንስ ወደዚህች ከተማ የመጣውከደቀ መዝሙሩ ከአብሮኮሮስ ጋር ነው፡፡ የስብከት ሥራቸውንበቀጥታ መጀመር ስላልቻሉም ሮምና የምትባል አንዲት ሞግዚትቤት ውስጥ ባሮች ኾነው ገቡ፡፡ እርሷም ዮሐንስን እንጨት ፈላጭ፣አብሮኮሮስን ደግሞ ውኃ ቀጅ አደረገቻቸው፡፡ አንድ ቀንከምታሳድጋቸው ልጆች አንዱን ይዛ ወደ ቤተ ጣዖት ስትገባዮሐንስና አብሮኮሮስ አብረዋት ገቡ፡፡ ያን ጊዜ በቤተ ጣዖቱ ያደረውሰይጣን እነ ቅዱስ ዮሐንስን ሲያይ የቤቱን ዕቃ አደናብሮ ወጣ፡፡አስከትላው የነበረው ልጅም በድንጋጤ ሞተ፡፡ ያን ጊዜ “የእናንተመምጣት ነው ለዚህ ኹሉ ያበቃኝ” ብላ ደበደበቻቸው፡፡ ቅዱስዮሐንስም “አስነሡልኝ አትዪምን?” ብሎ መለሰላት፡፡ “ያሁኑ ይባስ!ከመቼ ወዲህ ነው ደግሞ የሞተ ሰው የሚነሣው?” ብላ የበለጠተቆጣች፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስና አብሮኮሮስ ጸሎት አቅርበውአስነሡላት፡፡ በዚህ ተአምር አምና ተጠምቃለች፡፡ በቤቷምየምእመናን ጉባዔ ተመሠረተ፡፡ እርሷም ለዚያ እመምኔት አድርገውሾሟት፡፡ ከዚያም በኤፌሶንና በአከባቢዋ ወንጌልን ለመስበክ ሰፊ በርተከፈተለት፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስ በኤፌሶን በሚያስተምርበት ጊዜ ከኔሮን ቄሣር ቀጥሎበሮም የነገሠው ድምጥያኖስ (፹፮-፺፮ ዓ.ም) የራሱን ምስል አሠርቶእንዲሰገድለት ወደ ኤፌሶን ላከ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን ከምእመናንጋር ኾኖ ይህን ድርጊት ተቃወመ፡፡ ከዚያም ወደ ሮም ተወሰደናበፍል ውኃ ተሰቃይቶ በመንግሥት ላይ ያመፁ ኹሉወደሚታሠሩባት በደሴተ ፍጥሞ እንዲታሰር ተፈረደበት፡፡ ራዕዩንያየውና የጻፈውም በዚያ ቦታ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ድምጥያኖስከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱና ወንጌሉንእንደ ጻፈ ይነገራል፡፡

    ስለ ቅዱስ ዮሐንስ የመጨረሻ ሕይወት ኹለት የተለያዩአመለካከቶች አሉ፡፡ አንደኛው በዮሐ.፳፡፳-፳፫ ላይ የተጻፈውንመነሻ በማድረግ “ዮሐንስ ሞትን አልቀመሰም” የሚል ሲኾንኹለተኛው ደግሞ በማር.፲፡፴፰-፴፱ የተጻፈውን ቃል በመጥቀስ“የጌታን የሞት ጽዋ ጠጥቷል፤ የሞትን ጥምቀት ተጠምቋል፤በግልጽ አነጋገር ሞቷል” የሚል ነው፡፡

    አባ ጀሮም ስለ ወንጌላዊው ሲገልጥ ዮሐንስ የመጨረሻውን በምድር የኖረበትን የዕድሜ ዘመን በኤፌሶን ከተማ እንዳሳለፈው ጽፏል፡፡ በዚህ ወቅትም እጅግ ከማርጀቱ የተነሣ “እርስ በራሳችሁ ተዋደዱ ይህ የጌታችን ትእዛዝ ነውና ይህን ከጠበቃችሁ ይበቃችኋል” የምትለዋን ቃል ብቻ ለደቀ መዛሙርቱ ይነግራቸው ነበር፡፡ ይህ የዮሐንስ የዘወትር ትምህርቱ ነው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም “አባታችን ለምን ኹል ጊዜ አንድ ዓይነት ትምህርት ታስተምረናለህ” ሲሉትም “ልጆቼ ይህ የጌታ ትእዛዝ ነው” በማለት ይመልስላቸው ነበር፡፡

    ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን የወንጌላዊው በዓል በየዓመቱ ጥር ፬ እና በየወሩ በ፬ እርሱ የደረሰው የቁርባን ምስጋና እንዲቀደስ ታዛለች፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስና የጌታ ሥዕል

    ለጌታችን ሥዕል ምንጭ ከኾኑት አንዱ ወንጌላዊ ዮሐንስ ነው፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለበት ዘመን የነበረው የሮማ ቄሣርጢባርዮስ ቄሣር ይባላል፡፡ የቄሣሩ ልጅም ታማሚ ነበር፡፡ ቄሣሩምየጌታን የማዳን ሥራ እየሰማና እነ ጲላጦስንም የጻፉለትን ደብዳቤእየተመለከተ “ከዚያ ደግ ሰው መቃብር ወስዶ ልጄን ማንባሳለመልኝ?” እያለ ይመኝ ነበር፡፡ በመጨረሻም ልጁን ወስደውበጌታ መቃብር ላይ ሲያኖሩት ከሕመሙ ስለተፈወሰለት ፍቅሩንለመግለጥ የጌታን ሥዕል የሚሥልለት ሰው ያፈላልግ ጀመር፡፡ከዚያ በኋላም ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ ተገኘና ልክ በዕለተ ዓርብእንዳየው አድርጐ ሥሎ ሰጠው፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስና አስቸጋሪው የሽፍቶች አለቃ

    አንድ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ከኤፌሶን ከተማ ተነሥቶ ክርስቲያኖችንለማስተማር ሲዘዋወር ወደ አንድ ትልቅ ከተማ ገባ፡፡ በዚያች ከተማየሚገኙ ምእመናንም ጊልስ ስለሚባልና በዐሥራዎቹ ዕድሜ ክልልስላለ አንድ ወጣት ታሪክ አጫወቱት፡፡ ወጣቱን በጣም ይወዱትስለነበርና እናትና አባቱ ስለሞቱ “የሚንከባከበውና የሚያስተምረውካጣ ሊበላሽ ይችላል” ብለው ለቅዱስ ዮሐንስ ነገሩት፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስም ይኽንን ሲሰማ ወጣቱ ጊልስን ወደ ከተማይቱ ጳጳስወሰደውና “እንደ ልጅህ ተንከባከበው፤ እውነተኛ ክርስቲያንምአድርገው” ብሎ ሰጠው፡፡ የከተማዋ ጳጳስም ደግ ስለነበረ ጊልስንበደስታ ተቀበለው፡፡ ዘወትርም ያስተምረውና ይንከባከበው ነበር፡፡በመጨረሻም የአከባቢው ምእመናን በተሰበሰቡበት ጊልስተጠመቀ፡፡

    ከዚህ በኋላ ግን ነገሮች መቀያየር ጀመሩ፡፡ እኒያ አባት ሥራ በጣምሰለበዛባቸው ጊልስን “መቼም ተጠምቋል” ብለው እንደ በፊቱመቆጣጠርና ማስተማሩን ተዉት፡፡ ጊልስም የለመደው የአባትነትፍቅር ሲያጣ ወደ ከተማ ወጣ ብሎ ከእኩዮቹ ጋር መቀራረብጀመረ፡፡ ጓደኞቹ ግን መልካም አልነበሩም፡፡ ጠጭዎች፣ቁማርተኞችና ተደባዳቢዎች ነበሩ፡፡

    አንድ ቀን ማታ በአንድ መጠጥ ቤት ውስጥ ጊልስና ጓደኞቹ ሲጠጡአመሹ፡፡ኹሉም ሰክረው በያሉበት ሲወደቁ ጊልስ ብቻውን ቀረ፡፡በመጨረሻም የኹሉንም የመጠጥ ሒሳብ ከፍሎ ያለውን ገንዘብጨረሰ፡፡ በነጋታው ጊልስ ለጓደኞቹ “ለእናንተ ስል ገንዘቤን ኹሉአባከንኹ፤ አሁን ባዶ ኪስ ሆኛለኹ” ብሎ ነገራቸው፡፡ ኹሉምሳቁበትና “ጅሉ ጊልስ! እኛ ገንዘብ ከየት የምናመጣ ይመስልኻል?ይልቅ የምታገኘውን አጋጣሚ ተጠቅመኽ ስረቅ” አሉት፡፡

    በዚህ መሠረት ጊልስና ኹለቱ ጓደኞቹ የአንድ ሰው ቤት ሰብረውገቡና ገንዘቡንና ጌጣጌጡን ዘረፉ፡፡ በዚህም የተነሣ ጊልስ “መስረቅማለት በጣም ቀላል ሥራ ነው” ብሎ አመነ፡፡ ከዚያ በኋላ ጊልስናጓደኞቹ የታወቁ ዘራፊዎች ኾኑ፡፡ እነርሱ ባሉበት መንገድ ማንምበጤና ማለፍ አይችልም ነበር፡፡ አንድ ቀን ሰው ሲደበድቡ ነፍሱበእጃቸው ስለ ጠፋች ጊልስና ጓደኞቹ ከተማዋን ጥለው ጠፉ፡፡ከጥቂት ጊዜ በኋላም የጊልስ ስም በአከባቢው እየገነነ ስለ መጣ ሰውኹሉ ይፈራው ጀመር፡፡ እርሱና ጓደኞቹ አላፊ አግዳሚውንአላስቀምጥ አሉ፡፡ መንገደኞች ኹሉ በሰላም መጓዝ፣ ነጋዴዎችምበጤና መነገድ አልቻሉም፡፡ ጊልስ አለቃቸው ነበር፡፡ መግደልናመዝረፍም የዘወትር ሥራቸው ኾነ፡፡

    ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን ቅዱስ ዮሐንስ ወደዚያች ከተማ መጣ፡፡እኒያን ጳጳስም ስለ ወጣቱ ጊልስ ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም በጣምአፍረውና አዝነው፡- “ያልከኝን አልሰማኹም፤ ያዘዝኸኝንምአልፈጸምኩም፡፡ ጊልስ ዛሬ ሰው ኹሉ የሚፈራው ወንበዴ ኾኗል፡፡ዛሬ አላፊ አግዳሚውን አያስቀምጥም፡፡ ይህ ኹሉ ግን የእኔ ስሕተትነው” በማለት በፊቱ አለቀሱ፡፡

    ቅዱስ ዮሐንስም ይህንን ሲሰማ በእጅጉ አዘነ፡፡ ወዲያውም ጊልስያለበትን ጠየቀና በፈረስ እየጋለበ ተጓዘ፡፡ የአከባቢው ምእመናን“ጨካኝ ናቸውና ይገድሉኻል” ቢሉትም አልተመለሰም፡፡

    በተባለው ቦታ ሲደርስም ኹለቱ ሽፍቶቹ አገኙት፡፡ ወዲያውምጩቤያቸውን መዝዘው ከፊቱ ቆሙ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ፍቅርበተሞላበት ንግግር “እርሱ የድሮ ጓደኛዬ ነውና ከመግደላችሁ በፊትእባካችሁ ወደ አለቃችሁ ውሰዱኝ?” አላቸው፡፡

    ሽፍቶቹም እየሳቁ ወደ አለቃቸው ዘንድ ወሰዱት፡፡ ጊልስ መጣ፡፡ቅዱስ ዮሐንስም በፍቅርና በፈገግታ ተመለከተው፡፡ ጊልስዐወቀው፡፡ ደነገጠ፡፡ ዘወር ብሎም መሮጥ ጀመረ፡፡ ያን ታላቁን ሰውዮሐንስን ፈራ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም “ልጄ ለምን ትሸሻለህ? እኔ አባትህነኝ ምንም የሚጐዳ መሣርያም አልያዝኩም” አለው፡፡ ያ ጨካኝየሽፍቶች አለቃ ምርር ብሎ አለቀሰ፤ አነባ፡፡ መሣርያውን ኹሉአምዘግዝጎ ጣለ፡፡ ጓደኞቹንም፡- “እኔ ወደ ጌታዬ መመለሴ ነውናደኅና ኹኑ” አላቸውና ከቅዱስ ዮሐንስ ኋላ ተፈናጥጦ ወደ ጥንቱቦታው ተመለሰ፡፡ ትቷት ሄዶ በነበረችይቱ ቤተ ክርስቲያንም ዕድሜልኩን እግዚአብሔርን እያገለገለ ኖረ፡፡

    የዘመኑ ማጅራት መቺዎች ከጊልስ ምን ይማሩ ይኾን?

    ቅዱስ ዮሐንስና ምሳሌው

    ቅዱስ ዮሐንስ ከአራቱ እንስሶች መካከል በንስር ይመሰላል፡፡በንሥር የመመሰሉ ምክንያትም እንዲህ ነው፡፡ በሥነ አንስርት(አሞሮች) ጥናት ሊቃውንት እንደሚነገረው ንስር ዐይኑ ፅሩይ ነው፡፡ወደ ላይ መጥቆ ይበራል፡፡ ወጥቶ ረቦ ቁልቁል በተመለከተ ጊዜምየሰናፍጭ ቅንጣት የምታኽል ሥጋ ብትኾንም አትሰወረውም፡፡ያቺን አንሥቶ ይመገባታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም አካልና ሕልውናተገልጦለት፣ ንጽሐ ሥጋ ንጽሐ ነፍስ ንጽሐ ልቡና ተሰጥቶት“ቀዳሚሁ ቃል” ብሎ ተናግሯልና፡፡ ይህም መጥቆና ረቅቆ የሚያስብልዑለ ስብከት መኾኑን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም ንስር በእግሩይሽከረከራል፤ በክንፍ መጥቆ ይበራል፡፡ በእግር እንዲሽከረከርዮሐንስም እንደ ወንድሞቹ “ወልደ እጓለ እምሕያው ከሰማይ ወረደተወለደ” እያለ ይጽፋል፡፡ በክንፍ መጥቆ እንዲበር እርሱም አካልከሕልውና ተገልጦለት “ቀዳሚሁ ቃል” ብሎ ተናግሯልና፡፡

    በዚህ ዕለት ቅዱሱ ሐዋርያ ከእናቱ ‪ማርያም_ባውፍልያ ከአባቱ ‪ ዘብዴዎስ መወለዱን ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች:: በረከቱ ይደርብን እኛንም በቅዱሱ ምልጃ ይማረን፡፡

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top