• በቅርብ የተጻፉ

    Saturday 21 November 2015

    ዘመነ ዮሐንስ “መስከረም ጠባ” /ሉቃስ ተሻረ ዮሐንስ ተሾመ


    ዲ/ን ዮሐንስ ደምስ

    መስከረም ጠብቶ ይላል ወታደር፤ ዘጠኝ ወር ክረምት የት ሔዶ ነበር? ይባላል በሥነ ቃል ዘመን ሲለወጥ ፡፡ ከሥነ ቃሉ የምንረዳው መስከረም ሁልጊዜ የአዲስ ቀን መምጣት አብሳሪ መሆኑን ለመናገር በጠዋት መስለው ጠባ ይሉና ያለፈው ዓመት ሁል ጊዜ በሌሊት መስለው ይናገራሉ፡፡ «ዘመን ተለወጠ» ስንል ምን ማለት ነው? ዘመንስ ምንድን ነው?

    ዘመን መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፤ በእርሱ /በዘመን ውስጥ ግን ብዙ ነገሮች የሚነሡበትና የሚያልፉበትን ነገር የሚያስተናግድ ሥርዐት ነው፡፡ ዘመንን ለፍጡርና ለፈጣሪ በማለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ ዘመን ወይም ጊዜ የተፈጠረው ለፍጡር ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ዘመንን ለመለየት /ለማወቅ የተፈጠሩ መሆናቸውን ይናገራል፡፡ /ዘፍ 1፡14/ ፈጣሪ ግን ከጊዜ ውጭ ነው፡፡ ይህም ማለት የዘመን መቁጠሪያዎቻችን ከመፈጠራቸው በፊት ነበርና መቁጠሪያዎችንም የፈጠራቸው ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡

    ስለዚህ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ከተፈጠሩበት «ዕለተ ረቡዕ» በፊት የነበረውን የፍጡር አኗኗር በጊዜ ይህን ያህል ነው ብሎ መናገር አይቻልም ለዚህ ነው ኢትዮጵያውያን የባሕረ ሐሳብ ሊቃውንት ቁጥር ከተጀመረበት በፊት ያሉት ቀናት «ዕለተ ጠቢባን» ብለው የሚጠሯቸው፡፡ ዕለተ ጠቢባን ማለት የጠቢቡ የሥላሴ ዕለቶች ማለት ነው ርዝማኔያቸውን ራሱ ባለቤቱ ያውቃል እንጂ ፍጡር አያውቃቸውም ለማለት ነው፡፡

    ታድያ ዘመን ተለወጠ ስንል ምን ማለት ነው? በባሕረ ሐሳብ ሊቃውንት ዘንድ አዲስ ዘመን ወይም አሮጌ ዘመን የለም፡፡ ፀሐይ ሁልጊዜም አካሔዷ አንድ ነው፡፡ ጨረቃና ከዋክብትም ሥርዓታቸውን ጠብቀው፤ የሚታዩበት ጊዜ ሳይሸራርፍ ይታያሉ፡፡ የተፈጠሩበትን ዓላማ ሲያስፈጽሙ ይኖራሉ፡፡ ይህ ሥርዐት ከተፈጠሩበት ዕለት ጀምሮ ያለ ነው፡፡ ስለዚህ ዘመን መለወጥን የምንናገረው በዚህ ለዘለዓለም ጸንቶ በሚኖር ሥርዐት ውስጥ የሚመላለሱ ዑደቶችን መናገር ማለት ነው፡፡ ዑደት ማለት ዞሮ መግጠም ማለት ነው፡፡

    በኢትዮጵያውያን የባሕረ ሐሳብ ሊቃውንት ዘንድ ሰባት /7/ ዓውዶች አሉ፡፡ የአንዱ ዑደት ሲፈጸም ሌላ ዑደት ይጀምራል፡፡ ለዚህም ነው ዘመን መጀመሪያ እና መጨረሻ የለውም የምንለው፡፡

    ሰባቱ ዓውዶች የሚባሉት፡- ዓውደ ዕለት በየሰባት ቀኑ የሚመላለስ፣ ዓውደ ወርኅ በ30 ቀኑ የሚመላለስ፣ ዓውደ ዓመት በጨረቃ 354 ቀን በፀሐይ በ365 ቀን እንዲሁም በከዋክብት በ364 ቀን የሚመላለስ፣ ዓውደ አበቅቴ በ19 ዓመቱ በ/19 ዓመት አንድ ጊዜ ፀሐይና ጨረቃ ጉዞአቸውን በጋራ የሚጀምሩበት /ተራክቦ የሚያደርጉበት/፣ ዓውደ ጳጉሜ በዐራት ዓመት የሚመላለስ /በዐራት ዓመት አንድ ጊዜ ጳጉሜ 6/ የሚሆንበት እንዲሁም በ600 ዓመት አንድ ጊዜ ጳጉሜ ሰባት ትሆናለች፡፡ ዓውደ ማኅተም በ76 ዓመት የሚመላለስ ሲሆን በ76 ዓመት ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ አበቅቴው ደግሞ 18 ይሆናል፡፡ ዓውደ ቀመር ይህ በ532 ዓመት የሚመላለስ ሥርዓት ነው፤ በዚህ ዓውድ ሁሉ ነገሮች ይገጣጠማሉ፡፡

    ኢትዮጵያ በእነዚህ ዐውዶች ዘመን ትቆጥራለች፡፡ ዓውድ የሚመላለስ ነው ብለናል፡፡ ስለዚህ የሚመለስ ከሆነ መነሻ የሚሆነው የቱ ነው የዓውደ ዕለት መነሻ ጥንተ ዕለት /የመጀመሪያ ዕለት/ የተባለው እሑድን አንድ ብለን እንቆጥራለን፡፡ ለዓውደ ዓመት መስከረምን ወር መነሻ አድርገን እንቆጥራለን፡፡ ለእነዚህ መነሻ ከአበጀንላቸው ሌላው ቀላል ነው፡፡ እሑድ ለምን መነሻ ሆነ ከተባለ የዕለታትን ስያሜ ማየት ተገቢ ይሆናል፡፡ እሑድ ማለት «አሐደ» ከሚለው ግስ የወጣ ሲሆን የመጀመሪያ ማለት ነው፡፡ «በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ» /ዘፍ. 1፡1/ እንዲል፡፡ ፍጥረት መፈጠር የተጀመረበት ዕለት ስለሆነ የሚል ምክንያት ይሰጡታል፡፡ ሰኞ «ሰኑይ» ከሚል ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን «ሁለተኛ» ማለት ነው፡፡ ማክሰኞ «ሠሉስ» በግእዙ ሠሉስ ይላል ሦስተኛ ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ ማክሰኞ ማለት /ማክ-ሰኞ/ ማለት የሰኞ ማግስት የሚል ትርጉም አለው ተመሣሣይ ነው፡፡ «ረቡዕ» ማለት ረቡዕ አራተኛ ሐሙስ አምስት አምስተኛ ማለት ሲሆን አርብ ግን ተለይቶ «ዐርበ» «መሸ» ከሚለው ግስ የወጣ ቃል ሲሆን «የፍጥረት መገባደጃ ሰው የተፈጠረበት ዕለት» ማለት ነው፡፡

    ከአርብ ቀጥሎ ያለው ዕለተ ሰንበት ተባለ ይህም ማለት ሰቡዕ ሰባተኛ ማለት ነው፡፡ ቀዳሜ የተባለው በሐዲስ ኪዳን ነው ትርጉሙም ቀዳሚት ሰንበት የመጀመሪያዋ ሰንበት ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም የሐዲስ ኪዳን ሰንበት እሑድ ነውና፡፡ ስለዚህ ስያሜያቸው ከዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ ባለው ቅደም ተከተል የተሰጠ እንጂ እንደ ምዕራባውያን እንዲሁ የተሰየመ አይደለም፡፡

    ስለዚህ እሑድ የዓውደ ዕለት መነሻ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሁሉም የሚመላለሱ ስለሆኑ አንዱን ቋሚ አድርጎ መቁጠር ግድ ይላል፡፡ የዕለታትስ ስማቸው ራሱ መነሻውን ያመለክታል መስከረም ለምን የዐውደ ዓመት መነሻ ሆነ የወራቶችን ስም ትርጉም በትክክል አይታወቅም፡፡ ዳሩ ግን መስከረም ከሌሎች ወራቶች የሚለይባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ምክንያት በዓመት መዓልቱና ሌሊቱ እኩል የሚሆኑባቸው ሁለት ወራቶች አሉ፡፡ /መስከረምና መጋቢት/ በትክክል ደግሞ በዓመት ሁለት ቀን ብቻ እኩል ናቸው /መስከረም 25 እና መጋቢት 25/ ስለዚህ መዓልቱና ሌሊቱ እኩል የሚሆንበትን ወር እንደ መነሻ ተጠቀሙ ማለት ነው፡፡

    እዚህ ላይ ግን ሌላ ጥያቄ ያስነሣል፡፡ መጋቢት ለምን አልሆነም የሚል ነገር ግን አሁንም ለመስከረም ሌላ ተጨማሪ ምክንያት አለ፡፡የመስከረም ቀኖችና የሚያዝያ ቀኖች አንድ ናቸው ማለትም መስከረም 1 ቀን ቅዳሜ ሲሆን ሚያዝያ 1 ቀንም ቅዳሜ ይሆናል፡፡ ይህም ማለት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መምህራን ጌታችን የተፀነሰው መጋቢት 29 ቀን በዕለተ እሑድ ነው ማለትም ዓለም በተፈጠረበት ቀን ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አዲስ ወር /ሚያዝያ/ የሚብተው የሚጀምረው ከሁለት ቀናት በኋላ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም የቀመር መጀመሪያ የሆነው ዕለት ማክሰኞ ሚያዝያ 1 ቀን ይሆናል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የሚያዝያን እንዳንጠቀም መዓልቱና ሌሊቱ እኩል አይደለም፡፡

    ይህን ተከትሎ በሚዞር ነገር መስማማት እንጂ ሁሉም መነሻ ሆኖ ማገልገል ይችላሉ፡፡ ለመስማማት ደግሞ በቂ ምክንያት ያስፈልጋል፡፡ሊቃውንት ደግሞ ብዙ ምክንያት ያለው መስከረም ስለሆነ መነሻቸው በመስከረም እንዲሆን አድርገዋል፡፡ የመጻሕፍት መምህራን ሌላ ምክንያት ይጨምራሉ፡፡ እስራኤላውያን ከግብፅ በወጡበት የሰባተኛው ወር መባቻ እንደሆነ እግዚአብሔር አዝዟል፡፡ ይኸውም መስከረም ነው ይላሉ፡፡ ክረምት በጨለማ በብሉይ ይመሰላል ፀሐይ የሚወጣበት መስከረም ደግሞ በብርሃን በሐዲስ ኪዳን ይመሰላል፤ ስለዚህ ለዓውደ ዓመት መነሻ ወር መስከረም ነው፡፡

    ይህን በመከተል፡-

    የኢትዮጵያውያን የዘመን መለወጫ መስከረም ነው፡፡መስከረም 1 ቀን ርእሰ ዓውደ ዓመት ተብሎ ይጠራል፡፡ ትርጉሙም ርዕስ የአንድ ጽሑፍ /ንግግር በር እንደሆነ ሁሉ በዓመት ውስጥ ያሉ ዓውደ ዓመቶች /በዓሎች/ እና አጽዋማት ማወቂያ /ማመላከቻው/ መስከረም 1 ቀን የሚውልበት ነውና፡፡ እንዲሁም የዓመቱ በዓላትና አጽዋማት የሚታወጀው መስከረም 1 ቀን ነው፡፡ በዚሁም ዕለት መዓልቱን /በፀሐይ/ ሌሊቱን /በጨረቃ/ በመቁጠር ምሥጋና ለእግዚአብሔር ይቀርባል፡፡ ለምሳሌ የ2008 ዓ.ም የመስከረም መባቻ አሥርቆትን እንመለከታለን፡፡

    በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
    በዛሬው ዕለት በፀሐይ 2008 ዓመት - መስከረም 1 ቀን
    በጨረቃ 2069 ዓመት ከ1 ወር ከ16 ቀን
    የሊሊቱ መባቻ - 24
    የጨረቃ መባቻ - 28
    የመዓልት መባቻ - 1
    ዕለተ ዮሐንስ 6 ቀን ያቀረብነው ምስጋና ተቀበል ብለው አባቶቻችን ለብቻ በመለየት ይጸልያሉ፡፡
    በዚህም የ2008 ዓ.ም አበቅቴ 22 መጥቅዕ ደግሞ 8 ነው፡፡ /አበቅቴና መጥቅዕ ተደምረው ከ30 አይበልጡም አያንሱም/ ዘመኑ ደግሞ ዘመነ ዮሐንስ ነው፡፡

    ኢትዮጵያውያን የአንድ ወር ርዝማኔን /የቀን ብዛት/ 30 ቀን በማድረግ እንቆጥራለን፡፡ ይኸውም በዋናነት የምንጠቀመው በፀሐይ ስለሆነ ነው፡፡ በፀሐይ አንድ ዓመት ማለት 365 ቀን ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዓት ነው ይህም ማለት የዓመቱ 12 ወሮች እኩል 30 30 ቀን ሆኖ 5 ቀን ከ6 ሰዓት ይተርፋል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ 13ኛ ወር ጳጉሜ መጨመር አስፈለገ፡፡ እንዲሁም 6 ሰዓት በአራት ዓመት /6x4/ 24 ሰዓት ይሁንና 1 ዕለት በጳጉሜ ላይ ይጨምራል ማለት ነው፡፡ ጳጉሜ 6 በሆነ ጊዜ ሠዓር ይባላል የጳጉሜ የመጨረሻ ዕለት /5/6ኛው/ ዕለት €œዕለተ ምርያን ይባላል፡፡ የገና /የልደት/ በዓል የሚውለው በዚህች ዕለት ነው፡፡ ስለዚህ የ2008 ዓ.ም በዓለ ገና /ልደት/ ዓርብ ዕለተ ታኅሣሥ 28 ቀን ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ጳጉሜ 6 ዓርብ ዕለት ስለሚውል ማለት ነው፡፡

    ማጠቃለያ፡- ዘመን ተለወጠ ማለት የሰው ልጅ መለዋወጥን መናገር እንጂ የፀሐይ፣ የጨረቃንና የከዋክብት መለወጥ መናገር አይደለም፡፡ ዘመን የተሠራው የሰው ልጅ መልካም እንዲሠራበት እና ለእግዚአብሔር በየሰዓቱ ምስጋና እንዲያቀርብበት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር አዲስ ዘመን ብለን በአከበርን ቁጥር እግዚአብሔር ለእኛ ለንስሐ እንጠቀምበት ዘንድ አንድ ዓመት ሰጠን ወይም ወደ ሞት እያቀረብን መጣን ማለት ነው፡፡ ዳዊት የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ በዘመኔ አጋማሽ አትውሰደኝ ያለው ለዚህ ነው፡፡ /መዝ. 101 ሥርዓታቸውን ጠብቀው ከሚኖሩ ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት የሰው ልጅ በሥርዐት መኖርን መማር ያስፈልጋል፡፡ ሉቃስ ተሻረ ዮሐንስ ተሾመ በማለት መስከረም መባቻ ላይ ቤተ ክርስቲያን ታውጃለች፡፡ ይህ ማለት ግን የአንዱ መሾም ለሌላው መሻር በሚለው የምድራውያን ሥርዐት ዓይነት አይደለም፡፡ አንዱ ወንጌላዊ ዘመኑን ለሌላው ወንጌላዊ መስጠቱን መናገር ነው፡፡

    ዘመነ ዮሐንስ የንስሐና የጽድቅ ሥራ የምንሠራበት ዘመን ይሁንልን አምላከ ዮሐንስ ተለመነን፡፡ አሜን፡፡

    • የተሰጡ አስተያየቶች
    • በፌስቡክ (Facebook) የተሰጡ አስተያየቶች

    0 comments:

    Post a Comment

    Item Reviewed: ዘመነ ዮሐንስ “መስከረም ጠባ” /ሉቃስ ተሻረ ዮሐንስ ተሾመ Rating: 5 Reviewed By: Getahun Amare - ጌታሁን አማረ
    Scroll to Top