Monday, 27 June 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፮ (የመጨረሻው )

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

✔ ጉባኤ ኦአክ ✔

በክፍል አምስት ለመግለጽ እንደተሞከረው ቴዎፍሎስ በቅዱስ ኤጲፋንዮስ አማካኝነት ሊያደርገው ያሰበው ነገር አልሰመረለትም፡፡ ነገር ግን በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ላይ እርሱ ራሱ ከሳሽና ዳኛ ለመኾን እጅግ ሲጨነቅና ሲጠበብ ቆይቷል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ነገሮች እንደ ድሮ እንዳሉ በማሰብ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ እንደ ወጣ ማለትም በዚህ በወርሐ ግንቦት አጋማሽ ላይ ስለ ሴቶች አለባበስ አስደናቂ የኾነ ስብከትን ሰበከ፡፡ አውዶክስያም ይህን ስብከት ሰማች፡፡ አንዳንድ ሰዎችም - በተለይ ሴቪሪያን የተባለ - ስብከቱ እርሷን ያነጣጠረ እንደ ኾነ ነገሯት፡፡ እጅግ ተናደደች፡፡ ይህንንም ይዞ ወደ አርቃድዮስ (ወደ ባለቤቷ) ሔደች፡፡ “እኔን ሰደበ ማለት አንተንም ሰደበ ማለት ነው” አለችው፡፡ ብዙዎቹ የታሪክ ጸሐፊዎች የቅዱስ ዮሐንስና የአውዶክስያ ግንኙነት የሚሻክረው በዚህ ምክንያት ነው ይላሉ፡፡

ያም ኾነ ይህ ነሐሴ መጨረሻ 403 ዓ.ም. ቴዎፍሎስ መጣ፡፡ እንዲመጣ ከተነገረው ከአንድ ዓመት በኋላ መኾኑ ነው፡፡ ከላይ እንደ ተናገርነው ቴዎፍሎስ ደጋፊ እያሰባሰበ በአዙሪት የመጣ ሲኾን አስቀድሞ ግን ሃያ ዘጠኝ ጳጳሳትን በባሕር ወደ ቁስጥንጥንያ ልኮ ነበር፡፡ በመኾኑም እርሱ በዚህ ጊዜ ሲደርስ ሞቅ አድርገው ተቀበሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ይህን ሰማ፡፡ ለጠብ እንደመጣም ተረድቶታል፡፡ ምንም ለጠብ እንደመጣ ቢያውቅም ግን ማረፊያ አዘጋጅቶለት ነበር፤ ቴዎፍሎስ አልመጣ ብሎ ወደ አውዶክስያ ሔደ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ነገር ሲናገር እንዲህ ብሏል፡- “እንደ ተለመደውና እንደ ትክክለኛ ሥርዓት ወደ ቤተ ክርስቲያን አልገባም፤ ወደ ቤተ መንግሥቱ ሔጄ ሰላም እንድለው እንኳን አልጠራኝም፡፡ ከዚህ ይልቅ ከእኔ ጋር ምንም ዓይነት ንግግር ወይም ጸሎት ወይም ሥርዓተ ቅዳሴ እንዳያደርግ ቆረጠ እንጂ፡፡ ከመርከብ እንደ ወረደ ምንም ሳይሳለም በቤተ ክርስቲያኑ በር አልፎ ሔደ፡፡ ለእርሱና አብረዉት ለመጡት አባቶች ብዬ ማረፊያ እንዳዘጋጀሁ ብነግረውም ተማጽኖዬን ንቆ ሔደ፡፡

ቴዎፍሎስ እንዲህ ገብቶ ለሦስት ሳምንታት ተቀመጠ፡፡ ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን የሚያጠቃበት መንገድ ለመዘየድ እንጂ፡፡ በዚህም ቅዱስ ዮሐንስን የሚጠሉ ሴቶችን አሰባሰበ፤ ቅዱስ ዮሐንስ ስለ ጌጠኛ ልብስ ያስተማረው ትምህርት እናንተን ሰድቦ ያስተማረው ነው በማለት፡፡ ከእነዚህ ሴቶች በተጨማሪ ሴቬሪያን እንዲሁም ፕቶሎሚያስ የሚባሉ ኹለት የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቀንደኛ ጠላቶችን አገኘ፡፡ እነዚህ ሦስቱ ቅዱስ ዮሐንስን ለማጥፋት ኅብረት ፈጠሩ፡፡ ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ አሁንም ቀጠለ፤ ወደ አውዶክስያ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ጌጠኛ ልብስን በማስመልከት ባስተማረው ትምህርት አኩርፋ ነበርና ቴዎፍሎስ ደግሞ ሲጨምርባት የልብ ልብ ተሰማት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን ለማጋዝ ከቴዎፍሎስ ጋር ተወዳጀች፡፡

ቅዱስ በዚህ ጊዜ በጣም ግራ ተጋብቷል፡፡ ቴዎፍሎስ ለጠብ እንደ መጣ ቢያውቅም የጠቡ መነሻ ምን እንደ ኾነ ሊገባው አልቻለም፡፡ እስኪ ከቃሉ እንስማው፡- “መልካም መስሎ የታየኝን ኹሉ አደረግሁ፡፡ ከገባባት ቅጽበት አንሥቼ ለከተማችን እጅግ የሚንቦገበግ እሳትን ይዞ ለመጣው (ቴዎፍሎስ) እንድንገናኝ፣ ለምን እንደ መጣ እንዲነግረኝ ደጋግሜ ጠየቅሁት፡፡”
ቅዱስ ዮሐንስ እንደ ቴዎፍሎስ ቢያስብ ሊያሸንፈው ይችል ነበር፡፡ ምክንያቱም እንደ ሕጉ ማለትም በጉባኤ ኒቅያ እንደ ተወሰነው አምስተኛው ቀኖና ከሔድን ቴዎፍሎስ ያለ አገረ ስብከቱ መጥቶ ነውና ይህን ኹሉ የሚያደርገው፡፡ “ነገር ግን” ይላል ቅዱስ ዮሐንስ “ይህን ላደርግ አልወደድኩም፡፡ እንደ አባቶቼ ሥርዓት አክብሬ ልቀበለውና ላስተናግደው አሰብኩ እንጂ፡፡”

በመጨረሻም መስከረም መጨረሻ ላይ ከላይ ስንገልጻቸው የነበሩ አካላት በኬልቄዶን አቅራቢያ ኦአክ በተባለ ሥፍራ አስቀድሞ የታሰበበት ሐሰተኛ “ሲኖዶስ” አዘጋጁ፡፡ ቁጥራቸው ሠላሳ ስድስት ሲኾኑ ሃያ ዘጠኙ ከቴዎፍሎስ ጋር ከግብጽ የመጡት ናቸው፡፡ እናም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲመጣና ፍርዱን እንዲሰማ መልእክት ላኩበት፡፡ ፕትርክናውን ስለማይቀበሉ መልእክት ሲልኩ “ለዮሐንስ” የሚል ነበር እንጂ “ለሊቀ ጳጳስ ዮሐንስ” አይልም፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን አልሔደም፡፡ “የጉባኤው” ሕገ ወጥነትን የሚገልጽ ደብዳቤም መልእክቱን ይዘው በመጡ ሰዎች ላከላቸው እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ እስኪመጣ ድረስ ብለው ግን ክሱን ይጽፉ ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀድሞ በምግባረ ብልሹነታቸው ክህነታቸውን የያዘባቸው ካህናትና እነቴዎፍሎስ ራሳቸው ይህን አረቀቁ፡፡ እነቴዎፍሎስ በ29 ነጥብ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ሲከሱት ይስሐቅ የተባለ መነኮስ ደግሞ በ17 ነጥብ ከሰሰው፡፡ እስኪ ከተከሰሰባቸው ነጥቦች ጥቂቶቹን እንመልከት፡- ንግሥቲቱን አልዛቤል ብሎ ሰድቧል [ኤልዛቤል ብሏታል ያሉት ንግሥቲቱ ካሊትሮጳ የምትባል ብእሲታ ማውታ መሬቷን ቀምታት ስለ ነበረችና እንድትመልስላት ስለ ገሠጻት ነው]፤ ካህናትን በድሏል [ገንዘብን ይሰርቁ የነበሩት ክህነታቸውን ስለያዘባቸው ነው]፤ አላስፈላጊ ናቸው በሚል በቤተ ክህነቱ የነበሩ ውድ ንብረቶችን ሸጧል፤ የሽያጩን ገንዘብ ወዴት እንደ ወሰደውም አናውቅም፤ ድግሶችን በማስቀረቱና ለብቻው ስለሚበላ እንግዳ ተቀባይነትን ንቋል፤ ደጋግመው ኃጢአት የሚሠሩ ሰዎች ደጋግመው ንስሐ እንዲገቡ ያስተምራል፤ አስቀድመው ቤተ ክርስቲያንን ሲጎዱ የነበሩ አሕዛብ ተቀብሎ ወደ ቤተ ክርስቲያን ጨምሯል፤ ወደ ታናሽ እስያ በመሔድ ጳጳሳትን ሾሟል፤ ኦሪገናዊ አስተምህሮ ያላቸውን ሰዎች ተቀብሏል፤ ከአጠገቡ ሌላ ሰው ሳይኖር ሴቶችን ይቀበላል የሚሉ ይገኙበታል፡፡

የመጀመሪያው ስደት

እንግዲህ በእነዚህና እነዚህን በመሰሉ ክሶች ራሳቸው ከሳሽ ራሳቸው ዳኛ ኾነው በሌለበት “ጉባኤ” እንዲህ ብለው በመወሰን ወደ ንጉሥ አርቃዲዮስ መልእክት ላኩ፡- “ዮሐንስ በጉባኤው እንዲገኝ ጠርተነው ነበር፡፡ ነገር ግን ጥፋቱን ስለሚያውቅ ሊመጣ አልወደደም፡፡ ስለዚህ በቀኖናው መሠረት በሕይወት ዘመኑ ኹሉ በግዞት እንዲኖር ወስነንበታል፡፡” ንጉሡ ወደሚወስንበት የግዞት ሥፍራ እንዲጋዝ የሚጠይቅ ሐተታ (ሪፖርት) ነበር፡፡ ንጉሡም ይህን አጽድቆ የሚያግዙትን ወታደሮች ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ላከ፡፡

ይህን ዜና የሰማው ሕዝብ ለመግለጽ በሚያስቸግር ኹኔታ ገነፈለ፡፡ ወደ ሃጊያ ሶፍያ ሮጠ፡፡ ለሦስት ቀንና ለሦስት ሌሊት ሙሉ ወታደሮቹ ቅዱስ ዮሐንስን እንዳያግዙ ከለከሏቸው፡፡ በኹለተኛው ቀን ላይ ግን ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ዓውደ ምሕረቱ ወጣ፡፡ ማስተማር ጀመረ፡፡ ስለ ድጋፋቸው በማመስገን በጸሎታቸው እንዲያስቡት ማለዳቸው፡፡ “እስከ ዓለም ፍጻሜ ከእናንተ ጋር ነኝ ያለው አምላክ አሁንም ከእኛ ጋር ነው” አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ፊትን አይቶ የማያዳላ መምህር ነውና ወደ ተግሣጽ ተሻገረ፡- የጴጢፋራ ሚስት ከዮሴፍ ጋር ዝሙት ለመሥራት እንዳደረገችው ኹሉ ዛሬም ግብጻውያን በቅዱሱ መንፈሳዊት ሙሽሪት (ምእመናን) ለመዳራት እዚህ ድረስ መምጣታቸውን፣ ዛሬም ሄሮድያዳ የመጥምቁ ዮሐንስን አንገት ሽታ እየዘፈነች እንደ ኾነ፣ ትናንት ከእርሱ እየተማረች 13ኛው ሐዋርያ ያለችው አውዶክስያ ዛሬ ግን ከአሳዳጆቹ ጋር ተስማምታ ይሁዳ እንደኾነችበት፣ ይህ ኹሉ ቢኾንም ግን እንደ ኢዮብ “የእግዚአብሔር ስም ለዘለዓለም የተባረከ ይኹን” ማለት እንደሚገባ አስተማረ፡፡ በቀጣዩ ቀን አመሻሽ ላይም በዘዴ ያለ ምንም ግርግርና ትርምስ ራሱን ለወታደሮቹ እጁን በመስጠት ወደ ስደት (ግዞት) በመርከብ ተሳፍሮ ሔደ፡፡

በጣም የሚገርመው ነገር ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ እነዚያን መነኮሳት ያባረራቸው በኦሪገናዊነት ነበር፡፡ ታሪክ ጸሐፊው ሶቅራጠስ እንዳለው ግን አሁን ይህን ኹሉ ረሳው፡፡ በቃ - እንዲሁ ታረቃቸው፡፡ ጥንቱም ቅዱስ ዮሐንስን መበ’ቀል እንጂ ዓላማው እነርሱ አልነበሩምና! ይሔ ብቻ አይደለም፡፡ የኦሪገንን መጻሕፍት ተቀብሎ ማንበብ ጀመረ፡፡ ይልቅ ወደ ተወዳጁ አባታችን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እንመለስ!
ሊቁ እንደተሰደደ አሳዳጁ ሴቬሪያን በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አትሮንስ ላይ ቆመ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ስደት የሚገባው መኾኑን “መስበክ” ጀመረ፡፡ ሕዝቡ ግን ተቈጣ፡፡ በእሳቱ ላይ ጋዝ ጨምሮባቸዋልና ገነፈሉ፡፡ አባታችንን መልሱልን አሉ፡፡ ከዚህም የተነሣ ቁስጥንጥንያ ከተማ በሁከት ተናጠች፡፡ ቤተ መንግሥቱ ተሸበረ፡፡

የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከመጀመሪያው ስደት መመለስ

በሚቀጥለው ሌሊት ደግሞ ጭራሽ ሌላ ነገር ተከሰተ፡፡ ከሕዝቡ አይደለም፡፡ ከላይ ከአርያም ቁጣ መጣ፡፡ ከተማዋ በከባድ የመሬት መንቀጥቀጥ ተናጠች፡፡ መሬት መንቀጥቀጡ ለየት ባለ መልኩ በአውዶክስያ መኝታ ቤት በረታ፡፡ ከዚህ የተነሣም ፍላሲላ የተባለች ልጇ ሞተች፡፡ አውዶክስያ ሥራዋን ታውቃለችና ይህ የእግዚአብሔር ቁጣ እንደ ኾነ በማወቅ አርቃድዮስን ማለደችው፤ ቅዱስ ዮሐንስ ከተሰደደበት በአስቸኳይ እንዲመለስ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን አሳምኖ ለማምጣትም ከሚንስትሮቿ አንዱን ደብዳቤ አስይዛ ላከችው፡፡ በደብዳቤዋ ላይ፡- ከእነዚያ ክፉዎች ጋር በመተባበር ላይ እጇ እንደሌለበት፣ ልጆቼን ያጠመቅህልኝ’ኮ አንተ ነህ በማለት ሊቁን እጅግ እንደምታከብረው ገለጸችለት፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ተመለሰ፡፡ ነገር ግን አለአግባብ በጉባኤ እንደተሰደደ ኹሉ በአግባብ በጉባኤ ሊመለስ እንደሚገባው በማመን ወደ ከተማዋ አልገባም፡፡ በሚዘገይባት እያንዳንዷ ቅጽበት ግን ሕዝቡ እንደገና በቤተ መንግሥቱ ላይ ዓመጹን እየጨመረ ስለሔደ ንጉሡ ይህን በመግለጽ እንዲገባ ለመነው፡፡ ቅዱሱም የሕዝቡን ቁጣ ለማብረድ ሲል ለመግባት ተገደደ፡፡

አሳዳጆቹ አፈሩ፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ መንበር ላይ ለመቀመጥ ቋምጠው የነበሩ ኹሉ ቀልባቸው ተገፈፈ፡፡ ሕዝቡም የቅዱስ ዮሐንስን መመለስ ሰምተው ወደ ሃጊያ ሶፍያ ተመሙ፡፡ እነዚያ ምግባር የለሽ መነኮሳት (እነ ይስሐቅ) ሕዝቡን በማሳሳት ሌላ ሁከት ለመፍጠር አስበው የነበረ ቢኾንም ወታደሮች መጥተው ነገሩን አበረዱት፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ቁስጥንጥንያ ሲመለስ ጥቅምት መጀመሪያ ላይ ነበር፡፡ ከሠላሳ በላይ ሊቃነ ጳጳሳት ተቀበሉት፡፡ ሕዝቡም ጧፍና ችቦ አብርተው በመዝሙርና በዕልልታ ተቀበሉት፡፡ ከደስታቸው ብዛት የተነሣም ተሸክመው ወስደው ከመንበረ ጵጵስናው አስቀመጡት፡፡ ንግግር እንዲያደርግ ግድ አሉት፡፡ ተነሣ፡፡ “የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይኹን” የምትለዋን የኢዮብ ቃል አዘውትሮ ይጠቅምባት እንደ ነበር ነገራቸው /ኢዮ.1፡21/፡፡ አሁንም ይህን ቃል ሊደግምላቸው እንደሚወድና ስለ ስደቱና ስለ መመለሱ እግዚአብሔርን ሊያመሰግን እንደሚፈልግ፣ ጠላቶቹ ከሚወዳቸው ልጆቹ ሊለያዩት ቢፈልጉም ይበልጥ ሌሎች ወዳጆችን እንዳፈራለት፣ አስቀድሞ ቤተ ክርስቲያኑ ብቻ ይሞላ እንደ ነበር አሁን ግን የከተማው አደባባዮች በሙሉ አብያተ ክርስቲያናት እንደ ኾኑ፣ ምንም እንኳን በዚያ ሰዓት ፈረስ እሽቅድምድም የነበረ ቢኾንም ተመልካቹ በሙሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንደ መጣ፣ የአብርሃም ሚስት ሣራ የግብጹ ንጉሥ ሊወስዳት እንዳሰበ የእርሱ ሙሽሪት (ምእመናንም) ቴዎፍሎስ ሊወስዳቸው ቢያስብም ሊሳካለት እንዳልቻለ፣ ልጆቹ በሙሉ እንዲህ ሲሰበሰቡ ተኩላዎቹ ግን መበታተናቸውን በመግለጽ፣ አውዶክስያም እንዲመለስ በማድረጓ በማመስገንና በዚህ ኹሉ እጅግ ደስ እንደ ተሰኘ ነገራቸው፡፡ ሕዝቡ ከመጠን ያለፈ ደስታም ስብከቱን ሳይጨርስ እንዲቀመጥ ኾኗል፡፡ በዚህ ጊዜ እነ ቴዎፍሎስ በጣም በመፍራት ሹልክ ሹልክ ብለው ጠፍተው ወደ አገራቸው ሔደዋል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ግን አሁንም እንደ አዲስ ጉባኤ ተደርጎ አለአግባብ መሰደዱን የሚገልጽና እንደገና እነ ቴዎፍሎስና አብረው የመጡት ጳጳሳት ባሉበት በአግባብ በጉባኤ ሊመለስ እንደሚገባ ለአርቃድዮስ ይገልጽለት ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ የሚለው ክብርን ፈልጎ ሳይኾን በኋላ “ሕጋዊ ኾነህ አልተመለስህም” ሊል የሚችል አካል እንዳይኖር ምክንያት ለማሳጣት ነው፡፡ አርቃድዮስ በዚህ በማመን ለቴዎፍሎስ መልእክት ልኮለታል፡፡ ቴዎፍሎስ ግን “በአሌክሳንድርያ ያሉ ልጆቼን ትቼ ብሔድ ዓመጽ ያስነሣሉ” በማለት ሊመጣ እንደማይችል ገለጸ፡፡ በመኾኑም እነ ቴዎፍሎስ ባይኖሩም ሌሎች ስድሳ ሊቃነ ጳጳሳት ተሰብስበው ቅዱስ ዮሐንስ ሕጋዊው የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ መኾኑንና የኦአክ ጉባኤን እንደሚያወግዙ በመግለጽ መለሱት፡፡ አርቃድዮስም በጉባኤው ተገኝቶ ነበር፡፡

ኹለተኛው ስደት

ምንም እንኳን ቴዎፍሎስ ወደ አገሩ ቢመለስም ከእርሱ ጋር እንዲተባበሩ ገዝቷቸው የነበሩና የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቀንደኛ ጠላቶች የነበሩ እነ ሴቬሪያን፣ አካክዮስና አንቲዮኮስ ግን በቁስጥንጥንያ ነበሩ፡፡ ለጊዜው ተደብቀው የነበረ ቢኾንም ወደ ከተማው ተመለሱ፡፡ መመለሳቸው ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ ሊቁ በመመለሱ በማፈራቸው ሊቁ ላይ ስሕተት በመፈለግ አሁንም እንዲሰደድ በመሻት እንጂ፡፡ ጊዜውም እነርሱ ከጠበቁት በላይ ፈጥኖ እንደመጣላቸው ዐዩ፡፡ ሕዳር አጋማሽ ላይ በሃጊያ ሶፍያ ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት አውዶክስያ የራሷን ሐወልት አሠራች፡፡ ተመልከቱ! ሊቁ ወደ መንበሩ የተመለሰው ጥቅምት መጀመሪያ ላይ ነበር፡፡ ኹለት ወር እንኳን አልሞላውም፡፡ እናም አንድ እሑድ ላይ ዝግጅት አዘጋጀች፤ የዘፈን ነው፡፡ ሙዚቃው፣ ዘፈኑ፣ ጫጫታው፣ ጭብጨባው የቤተ ክርስቲያኑን አገልግሎት ረበሸ፡፡ በዚያ ሰዓት ቅዱስ ዮሐንስ እየቀደሰ ነበርና፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በዚህ ዕለት የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ሰማዕትነት በማስታወስ፡- አሁንም ሄሮድያዳ እየተቈጣች፣ እየዘፈነች፣ የዮሐንስን ራስ በውጭት እየፈለገች መኾኗን አስተማረ፡፡ ምንም እንኳን ስሟን ጠቅሶ ባይናገርም ዕለቱ ከመጥምቁ ዮሐንስ ጋር ስለ ገጠመ ስብከቱን እንደ ኹልጊዜ ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ ያስተምር ነበር፡፡ ንግሥቲቱ ግን ንግግሩ ኹሉ እርሷን የተመለከተ ኾነ በማሰብ ተበሳጨች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን የሚያሳድድ ሌላ ጉባኤ እንዲዘጋጅም ዐቀደች፡፡ ወደ ቴዎፍሎስና እርሱን ወደ መሰሉ ሌሎች ጳጳሳት ደብዳቤ በመላክም እንዲሰበሰቡ ጠራቻቸው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሥጋ እንዳየ ንሥር ከየአቅጣጫው ተሰባሰቡ፡፡ ቴዎፍሎስ ግን አስቀድሞ ያገኘው ሐፍረት ያውቃልና ነገሮችን በግብጽ ኾኖ ማሤሩን መረጠ፡፡

የገና በዓል ደረሰ፡፡ ከዚህ በፊት ንጉሡና ንግሥቲቱ በጌታችን ልደት በዓል ዕለት በሃጊያ ሶፊያ ቤተ ክርስቲያን እየተገኙ ያስቀድሱ ነበር፡፡ ዛሬ ግን በኦአክ ጉባኤ ጥፋተኛ የተባለ ጳጳስ በሚቀድስበት ቤተ ክርስቲያን መገኘት እንደማይችሉ አርቃድዮስ ለቅዱስ ዮሐንስ መልእክት ላከበት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስና ቤተ መንግሥቱ እንዲህ ሳይግባቡ እስከ ፋሲካ 404 ዓ.ም. ድረስ ቆዩ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ግን አሁንም ትምህርቱን እያስተማረ ነው፡፡ እነዚያ እርሱን ለማሳደድ ድጋሜ በአውዶክስያ የተጠሩት ጳጳሳት ግን በምን ምክንያት ሊያሳድዱት እንደሚገባ በየጊዜው ይሰበሰባሉ፤ ምንም ምክንያት አጡበት እንጂ፡፡ ይጠብቁ የነበረው የተንኮል ዘዴ የማያጣውን የቴዎፍሎስን ሤረኛ ዘዴ ብቻ ነበር፡፡ ቴዎፍሎስ አሁን አንድ ዘዴ አገኘ፡፡ በወርሐ ግንቦት 341 ዓ.ም. ላይ በአንጾኪያ የወጣ ቀኖና ነበር፡፡ ቀኖናዉን ያወጡት ግን አርዮሳውያን ጳጳሳት ናቸው፡፡ ጊዜ ከተወሰኑት ቀኖናዎች መሠረት አራተኛው ቀኖና፡- “በትክክለኛ ምክንያት ይኹን በግፍ ከመንበሩ እንዲወርድ ከተወሰነበት በኋላ ያው ሲኖዶስ ሳይመልሰው ወደ መንበሩ ቢመለስ መጀመሪያ በተወሰነበት መሠረት ስደቱ የጸና ነው” ይላል፡፡ እነዚህ አርዮሳውያን ይህን ቀኖና ያወጡት ቅዱስ አትናቴዎስን ከመንበሩ ለማሳደድ ብለው የወሰኑት ነው፡፡ ቴዎፍሎስ ግን በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ላይ ምክንያት ቢያጣ ለማጥቃት ሲል ብቻ የአርዮሳውያን ቀኖና ጠቀሰ፡፡ ተመልከቱ! በመጀመሪያው ስደት ላይም ልክ እንደዚሁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ለማሳደድ ሲል ብቻ የኦሪገን ትምህርትን ጠቀሰ፡፡ አሁንም እንደዚሁ የአርዮሳውያንን ቀኖና በኦርቶዳክሳዊው አባት ላይ ጠቀሰ፡፡

በዚህ ጊዜ ግን አሳዳጆቹ ተጨነቁ፡፡ ምክንያቱም በአንድ መልኩ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲሰደድ ይፈልጋሉ፤ በሌላ መልኩ ደግሞ ቅዱስ ዮሐንስን የሚያሳድዱት ቴዎፍሎስ በጠቀሰው ቀኖና መሠረት ከኾነ አርዮሳውያን እንደሚያስብላቸው አሰቡ፡፡ በዚህ መኻል የቴዎፍሎስን ምክር ላለመቀበል ወሰኑ፡፡ ይህም ቢኾን ግን ንጉሡ ሊቁን እንዲያሳድደው መወትወታቸውን አላቆሙም፡፡

በዓለ ትንሣኤ ሲቃረብ ንጉሥ አርቃድዮስ ወደ አፈወርቅ መልእክት ላከ፡፡ ትእዛዝ ነበር፡፡ “ከእንግዲህ ወዲህ በሃጊያ ሶፍያ አገልግሎትህን መስጠት አትችልምና አቁም” የሚል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን፡- “ቤተ ክርስቲያን በአደራ የተሰጠችኝ ከእግዚአብሔር እንጂ ከአንተ አይደለችም” በማለት ማስተማሩን ቀጠለ፡፡ በሕዝቡና በወታደሮች መካከል ደም ማፋሰስ ሊያመጣ ሲል ግን በመንበረ ጵጵስናው ተወስኖ ተቀመጠ፡፡

ሰሞነ ሕማማት እንደ ተጀመረ ሊቀ ጳጳሳቸው ቅዱስ ዮሐንስ በመንበረ ጵጵስናው ውስጥ የቁም እስረኛ መኾኑንና በበዓለ ትንሣኤ በካቴድራላቸው እንደማይገኝ ዐወቁ፡፡ ዓርብ ስቅለት ላይ አርባ የሚኾኑና ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን የሚደግፉ ጳጳሳት ንጉሡና ንግሥቲቱ ሊቁን ወደ አገልግሎት እንዲመለስ ለመኗቸው፡፡ አውዶክስያ ግን ሰድባ መለሰቻቸው፡፡ ከዚህም የተነሣ ከጳጳሳቱ ጳውሎስ የሚባል አንዱ እግዚአብሔርን ልትፈራ እንደሚገባና በልጆቿ ላይ ቁጣን ሊያመጣ የሚችል ማንኛውም ዓይነት ነገር ከማድረግ እንድትቆጠብ ገሠጻት፡፡

በዓለ ትንሣኤ ደረሰ፡፡ ዕለቱም እሑድ ሚያዝያ 17 ነበር፡፡ በዋዜማው ማለትም በ16 ንዑሰ ክርስቲያኖች ለመጠመቅ ተዘጋጁ፡፡ አገልግሎቱም በሀጊያ ሶፊያና በሃጊያ ኢሬኔ ይደረግ ጀመር፡፡ ሊቂዮስ በሚባል አሕዛባዊ መሪ የሚመሩና 400 የሚኾኑ የተመለመሉ ወጣቶች ወደ አብያተ ክርስቲያናቱ ገቡ፡፡ ጳጳሳቱና ካህናቱ አገልግሎቱን እንዲያቆሙ ነገሯቸው፡፡ ኃይልን በመጠቀምም ተጠማቂዎቹን ደበደቧቸው፤ ለመጠመቅ ውኃው ውስጥ ዕራቁታቸው የነበሩት ሴት ተጠማቂያን ያለ ልብስ ሸሹ፡፡ የመጠመቂያው ውኃ ወደ ደም ተለወጠ፡፡ የምሥጢረ ቁርባን ንዋያተ ቅዱሳት በአሕዛብ ወታደሮች ረከሱ፡፡ ካህናቱ ልብሰ ተክህኖአቸውን እንደ ለበሱ ወደ ከተማው ተሰደዱ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ራሱ ኹለት ጊዜ ከተቃጣበት ሞት ተረፈ፡፡ ደጋፊዎቹ ናቸው የተባሉ ኹሉ ወደ እስር ቤት ተወሰዱ፡፡ እንኳንስ በአካል ተገኝቶ በዓይነ ሕሊና እንኳን ሲያስቡት የሚያሰቅቅ ግፍ ተፈጸመባቸው፡፡ ይህን በቅርብ ርቀት ኾነው ያስፈጽሙ የነበሩት የቅዱስ ዮሐንስ ቀንደኛ ጠላቶች አንቲዮኮስ፣ አካኪዮስና ሴቬሪያን ናቸው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ለኹለት ወራት ሙሉ እንዲህ የቁም እስረኛ ኾኖ ቆየ፡፡ በዓለ ኃምሳ እንዳለፈ ቀጥላ በነበረችው ሐሙስ ማለትም ሰኔ 9 ላይ ግን አንቲዮኮስ፣ አካኪዮስ፣ ሴቬሪያንና ሲሪኖስ ትዕግሥታቸው ተሟጠጠ፡፡ ንጉሥ አርቃድዮስ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ስደት እንዲያጸድቅ ጫና አሳደሩበት፡፡ ንጉሥ አርቃድዮስ እስከ አሁን ድረስ ስደቱን ያላጸደቀው እንደ መጀመሪያው ስደት ሁከት ይነሣል ብሎ ፈርቶ ነው፡፡ በመጨረሻ ግን ሰኔ 20 ቀን 404 ዓ.ም. አመሻሽ ላይ ከአርቃድዮስ አንድ መልእክተኛ ተላከ፤ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ፡፡ ወዲያውኑ ቤተ ክርቲያኒቱንና ከተማይቱን ለቆ ወደ ስደት ሊወጣ እንደሚገባው ወደ ውሳኔ መድረሱን የሚያሳወቅ ነበር፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ሊቀ ጳጳሳቱን ሰብስቦ የመጨረሻ ንግግርና ጸሎት አደረገላቸው፡፡ ዕረፍት ላደርግ ነውና እዚህ ቆዩኝ ብሎም ኦሎምፒስንና እርሷን የሚመስሉ ታማኝ አገልጋዮችን እንዲህ አላቸው፡- “የእኔ ጉዳይ ወደ ፍጻሜ እንደ ደረሰ ይታየኛል፡፡ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፡፡ ከአሁን በኋላ ፊቴን የምታዩ አይመስለኝም፡፡ እናንተን የምጠይቃችሁ አንድ ነገር ብቻ ነው፡- ለቤተ ክርስቲያን የምታደርጉትን አገልግሎት ማንም እንዳያሰናክላችሁ፡፡ አገልግሎታችሁን ቀጥሉ፡፡ በእኔ ቦታ የሚተካው ሰው እርሱ ሹመት የማይፈልግና እርሱ ፈቅዶ ሳይኾን በኹሉም ስምምነት የሚሾም ከኾነ ልክ እንደ ዮሐንስ አድርጋችሁ ተቀበሉት፡፡ ለእኔ እንዳደረጋችሁት ለእርሱም አድርጉለት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያለ ጳጳስ ልትኾን አይገባምና፡፡ እንዲህ ብታደርጉ ምሕረትን ታገኛላችሁ፡፡ እኔንም በጸሎታችሁ አስቡኝ፡፡

በዚህ ጊዜ ኹሉም በኀዘን ተዋጠ፡፡ ግማሹ ያለቅሳል፤ ግማሹ በአሳብ ተውጦ ሰማይ ሰማዩን ያያል፡፡ እነ ኦሎምፒያስ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እግር ሥር ወድቀው ያለቅሳሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ከካህናት አንዱን ጠርቶ በዙርያ ያለው ሕዝብ ኹኔታውን ሰምቶ ረብሻ እንዳይፈጥር እንዲወስዳቸው ነገረው፡፡ በምዕራብ በኩል እርሱን ይጠብቁ ወደ ነበሩት ምእመናን ከመውጣት ይልቅም ደም ማፋሰስ እንዳይኾን ከቤተ ክርስቲያኑ ምሥራቅ አቅጣጫ ወጥቶ ለወታደሮቹ እጁን ሰጠ፡፡

በስደቱ ምን ምን እንደ ገጠመው በቅርቡ በታተመውና “ወደ ኦሎምፒያስ የተላኩ መልእክታት” በሚለው መጽሐፍ እንድትመለከቱ እጋብዛችኋለሁ፡፡

ዕረፍቱ 

ሞቱን ለሚናፍቁ አሳዳጆቹ ኹሉ ዕድሜው ረዘመባቸው፡፡ በመንገድ ላይ በሕመም ወይም በአየር ኹኔታው ተለዋዋጭነትና ቅዝቃዜ ከዚህ ከተረፈም አይሲያራውያን በተባሉ ዘላኖች ተገድሎ ይሞታል ብለው ጠብቀው ነበር፡፡ ይህ ግን አልኾነም፡፡ ይባስ ብሎም በዚያ ኩኩሰስ በተባለና ለስድት በተመረጠለት ቦታ ኾኖ በኦሎምፒያስ አማካኝነት በቁስጥንጥንያና በዙርያዋ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ማስተዳደሩን ቀጥሏል፡፡

በመኾኑም በዚህ እጅግ በመናደድ ፈጥኖ ይሞት ዘንድ ከቤተ መንግሥቱ ኹለት ወታደሮችን አስላኩ፡፡ ሰኔ አጋማሽ 407 ዓ.ም. ላይ ኩኩሰስ ደረሱ፡፡ ለሦስት ወር ያህልም በእግር እንዲጓዝ አደረጉት፤ በትኅርምት ባለቀ ሰውነቱ እንዲሞት ነበር፡፡ በመጨረሻም መስከረም 14 ቀን 407 ዓ.ም. በአርማንያ ባሲሊቆስ በተባለ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሥጋዉንና ክቡር ደሙን ተቀብሎ በ60 ዓመቱ ነፍሱን ለእግዚአብሔር ሰጠ፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ የተናገራት ቃልም፡- “ስለ ኹሉም ነገር ክብር ለእግዚአብሔር ይኹን” የሚል ነበር፡፡
ዕለተ ዕረፍቱን በተመለከተ በየአብያተ ክርስቲያናት ልዩነት አለ፡፡ በእኛ ቤተ ክርስቲያን የሚከበረው ግንቦት 12 ነው፡፡ ስለ ልዩነቶቹ መረዳት የሚፈልግ ካለ የኅዳር 17 ቀን ስንክሳር መመልከት ይችላል፡፡
የቅዱሱ ሰውነት ወደ ቁስጥንጥንያ የተመለሰው ከሠላሳ ዓመት በኋላ ሲኾን ያረፈውም በሃጊያ ኤሬኔ ነው፡፡

አነሣስቶ ላስጀመረን አስጀምሮም ላስፈጸመን እግዚአብሔር ክብር ኃይል ወእዘዝ ለዓለም ወለዓለም አሜን!!!

ምንጭ:- መቅረዝ ዘተዋሕዶ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፭

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ተዋዳጆች ሆይ! ክፍል አምስትን ሳላቀርብላችሁ ዘገየሁ፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝ፡፡ ከዓቅሜ በላይ የኾነ ጉዳይ ገጥሞኝ ነው፡፡

† ቁስጥንጥንያ ከተማ †

እስኪስለ ቁስጥንጥንያ ጥቂት እንበል! ከአንጾኪያ ይልቅ ቁስጥንጥንያ ከቤተ ክርስቲያናዊም ኾነ ከፖለቲካዊ ፋይዳዋ ከፍ ያለ ነው፡፡ መሥራቿ ታላቁ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ነው፤ በ330 ዓ.ም.፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን ከአራት መቶ እስከ አምስት መቶ ሺሕ ኗሪ ነበራት፡፡ መንበረ ፓትሪያሪኩ ለቤተ መንግሥቱ በጣም ቅርብ ነው፤ ሃጊያ ሶፍያ (ቅድስት ጥበብ - መድኃኔ ዓለም በሉት፡፡ ጥበብ ክርስቶስ ነውና)፡፡ በከተማይቱ ሦስት አብያተ ክርስቲያናት ነበሩ፡- በ381 ዓ.ም. ጉባኤ ቁስጥንጥንያ የተካሔደበትና ከሃጊያ ሶፍያ 150 ሜትር ገደማ የሚርቀው ሃጊያ ኢረነ (ቅድስት ሰላም)፣ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ የቅዱሳን ሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም በዮሐንስ መጥምቅ ምትረተ ርእስ የተሰየመ ቤተ ክርስቲያን ናቸው፡፡ በቅዱሳን ስም ቤተ ክርስቲያንን መሰየም የቅርብ ዘመን ታሪክ እንዳልኾነ እያስተዋላችሁ ነውን?

             
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅና ዲያቆናዊት ኦሎምፒያስ

ኦሎምፒያስማን እንደ ኾነች በቅርቡ በታተመው መጽሐፍ ይመልከቱ፡፡ አሁን ግን እዚህ መግለጽ ወደምንፈልገው እንመለስ፡፡ ከሃጊያ ሶፊያ ደቡባዊ አቅጣጫ የመነኮሳይያት መኖሪያ ነበር፡፡ እመምኔታቸውም ዲያቆናዊት ኦሎምፒያስ ነበረች፡፡ ድኾችን ትረዳለች፡፡ አብያተ ክርስቲያናትን ታሳንጻለች፡፡ ለመንፈሳዊያን አባቶች በሚያስፈልጋቸው ነገር ኹሉ ትረዳቸዋለች፡፡ ለራሷ ግን ምንም እንኳን እጅግ በጣም ባለጸጋ ብትኾንም የትኅርምት ሕይወትን የምትኖር ነበረች፡፡ የቅዱስ ዮሐንስና የኦሎምፒያስ ሕይወት በጣም ተመሳሳይ ነው፡፡ የተማረች ነች፡፡ ዕለት ዕለት ቅዱሳት መጻሕፍትን ታነባለች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም እንደዚሁ፡፡ እናም ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ቁስጥንጥንያ እንደ መጣ ከኦሎምፒያስ ጋር ተዋወቀ፡፡ መተዋወቅ ብቻ ሳይኾን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ልብሱን የምታጥብለት፣ በትኅርምት ለተጎዳ ሰውነቱ ተስማሚ ምግብን የምታዘጋጅለት እርሷ ነበረች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በቁስጥንጥንያ እንደ እርሷ የሚወደው የልቡንም የሚያጫውተው ሰው አልነበረም፡፡

ለውጥ በቁስጥንጥንያ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቁስጥንጥንያ እንደ መጣ ጊዜ አላጠፋም፡፡ እውነተኛ ትምህርቱን በመንበረ ቁስጥንጥንያም ወዲያው ቀጠለ እንጂ፡፡ የመጀመሪያ ተግባሩን ያደረገውም በሶሪያና በሮም ብሎም በእስክንድርያ የነበረውን ልዩነት መፍታት ነበር፡፡ በዚህም ለሊቀ ጳጳሳት መላጥዮስንና ፍላቭያንን ሳይኾን ለጳውሊኖስ ዕውቅናን ሲሰጡ የነበሩት ሮምና እስክንድርያ በቅዱስ ዮሐንስ አማካኝነት ዕርቅን ፈጠሩ፤ ወደ አንድነት መጡ፡፡ ቁስጥንጥንያ ሔዶ የአንጾኪያን ችግር ፈታ፤ እጅግ የሚያከብረው ሊቀ ጳጳስ ፍላቪያንም በሮምና በእስክንድርያ ዕውቅና እንዲሰጠው አደረገ፡፡
ይህንበድል አጠናቀቀ፡፡ አሁን ደግሞ ፊቱን ወደ አዲሱ መንበረ ጵጵስናው አዞረ፡፡ ከላይ የገለጽነውን የአንጾክያ፣ የሮምና የእስክነድርያ ችግር እስኪፈታ ድረስ ለጥቂት ጊዜያት የቁስጥንጥንያን መንበረ ጵጵስና ታዝቦታል፡፡ መታዘብ ብቻም ሳይኾን አስቸኳይ ለውጥ እንደሚያስፈልገው ተረዳ፡፡ ለውጡንም ከቤተ ክህነቱ ግቢ ጀመረ፡፡ የመጀመሪያው ለውጥ ያደረገውም ገንዘብ ነክ ነገሮችን ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያንን የማይጠቅሙ አላስፈላጊ ወጪዎችን አስቀራቸው፡፡ በቤተ ክህነቱ ውስጥ የሚደረጉ ግብዣዎችንና ድግሶችን ቤተ ክርስቲያንንና ድኾችን እንደ መዝረፍ አድርጎ ተመለከተው፡፡ ኹሉንም አስቀራቸው፡፡ ድሮዉንስ ከዮሐንስ አፈወርቅ ከዚህ ውጪ ምን ይጠበቃል? ምንም እንኳን እንዲህ አጀብን በሚወዱ ወገኖች ባይወደድለትም የቤተ ክርስቲያን ወጪ ወደ ድኾችና ወደ እጓለ ማውታን ዞረ፡፡

ፓትሪያሪኩ አሁንም ቀጠለ፤ ወደ ካህናት! ሥርዓት የለሾችንና ምግባረ ብልሹዎችን ሥርዓት እንዲይዙ አደረገ፡፡ በጣም የሚያስደንቀው ደግሞ ሊቁ እጅግ የሚወዳት ዲያቆናዊት ኦሎምፒያስንም መገሠጹ ነው፡፡ ለዚህስ አይደል፡- “መምህር ወመገሥጽ ዘኢያደሉ ለገጽ” የሚባለው? እናም ስትመጸውት አግባብ ባለው መልኩ እንድትመጸውት፣ ላልተቸገሩ ሰዎች ገንዘቧን እንዲሁ መስጠት እንደሌለባት እንዲያውም በራሱ አገላለጽ፡- “ጥቂት ውኃን ወደ ባሕር እንደ መጨመር” እንደ ኾነ ነግሯታል፡፡
በመቀጠልምወደ ምእመናን ዞረ፡፡ ቅጥ ያጣ አኗኗራቸውን እንዲያስተካክሉ ገሠጻቸው፡፡ ከአንዳንዶች በስተቀርም ሕዝቡ በጣም እየወደደው መጣ፡፡ ሕዝቡ ብቻ ሳይኾን በቤተ መንግሥቱም ቢኾን እየተከበረ መጣ፡፡

ስብከተ ወንጌሉንም በሃጊያ ሶፊያ፣ በሃጊያ ኢሬኔ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን፣ እንዲሁም የሰማዕታት ዓፅም ባረፉባቸው ቅዱሳን መካናት እየተዘዋወረ አስተማረ፡፡ ሕዝቡ በጣም እየወደደው መጣ፡፡ እንዲያውም ታሪክ ጸሐፊው ሶዜሜን እንደሚለው ብዙ ሰው እየተረገጠ ይጎዳ ነበር፡፡ የሊቁን ትምህርት ለመከታተል ይመጡ የነበሩት መናፍቃንም ጭምር ነበሩ፡፡ ምንምእንኳን በአንጾኪያ ካስተማረው ይልቅ በመጠኑ አነስ ያለ ቢኾንም አዳዲስ ትምህርቶችም ነበሩበት፡፡ ብዙዎቹ በዓላትን የተመለከቱ ስብከቶቹ፣ አብዛኛውን የሐዋሪያት ሥራ ማብራርያን፣ የተቀሩት የቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት ማብራሪያዎች እና ሌሎችም በዚህ ጊዜ ያስተማራቸው ናቸው፡፡ በከተማይቱ ብቻ ሳይኾን ወደ ገጠርም እየሔደ ያስተምራቸው ብሎም አብያተ ክርስቲያናትን እንዲያንጹ፣ እሑድ እሑድ ወደ ቅዱስ ቁርባን እንዲቀርቡ ያበረታታቸው ነበር፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሕሙማንንና ድኾችንም በየጊዜው ይጎበኝ ነበር፡፡ ወደ ኤፌሶንና ጎትስ ወደ ተባሉ አሕዛብም ሔዷል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅና የአራቱ መነኮሳት ነገር

የዚህጽሑፍ ዳራ ገድቦኝ በመኻል የዘለልኩት ብዙ ነገር አለ፡፡ አሁን ግን ወደ 401 ዓ.ም. ላምጣችሁ፡፡ በዚህ ዓ.ም. ወደ መኸር ወቅት በቁስጥንጥንያ ጎዳናዎች ላይ ወደ ኃምሳ የሚደርሱ መነኮሳት ታዩ፡፡ ከግብጽ የመጡ ናቸው፡፡ መሪዎቻቸው አራት ናቸው፡፡ ዲዮስቆሮስ፣ አውኖሚዮስ፣ አውሳብዮስና ኢዩትሚዮስ ይባላሉ፡፡ እንዲያውም ዲዮስቆሮስ ሊቀ ጳጳስ ነበር፤ ከአሌክሳንድርያ በደቡብ ምሥራቅ 60 ኪ.ሜ. በሚርቅ ቦታ! በኦርቶዶክሳዊ እምነታቸው በጣም የታወቁ ናቸው፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት ግን በፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ ኦሪገናውያን ተብለው ተከሰሱ፡፡ መከሰስ ብቻ ሳይኾን ከግብጽ ብሎም ከፍልስጥኤም ተባረሩ፡፡ ኦሪገናውያን ያስባላቸው “እግዚአብሔር ረቂቅ እንጂ እንደ ሰው ሰብአዊ ገጽታ የለውም” የሚለው እምነታቸው ነበር፡፡ ያም ኾነ ይህ በብዙ እንግልት ቁስጥንጥንያ ደረሱ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን አገኙት፡፡ በጉልበቱ ሥር ወደቁ፡፡ ጉዳያቸውን አስረዱት፡፡ ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስን እንዲማልድላቸውም ለመኑት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በጣም ተጨነቀ፡፡ በአንድ መልኩ ሲታይ ጉዳያቸው መታየት ያለበት በአገረ ስብከታቸው ሊቀ ጳጳስ ነው፤ በአሌክሳንድርያ፡፡ በሌላ መልኩ ሲታይ ደግሞ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ ሊመልሳቸው ቢያስብ መነኮሳቱ ቴዎፍሎስን በንጉሡ ዘንድ ሊከሱት እንዳሰቡ ነግረዉታል፡፡ በመኾኑም ምን ማድረግ እንዳለበት በማሰብ ተጨነቀ፡፡ ነገሩ ወደ ንጉሡ ከሚሔድ ይልቅም ቴዎፍሎስን መጠየቅ የተሻለ እንደ ኾነ ወሰነ፡፡ ስለኾነም ይቀበላቸው ዘንድ እጅግ ትሕትናን በተመላ መልኩ መልእክት ላከበት፤ ወደ ቴዎፍሎስ፤ እንዲህ በማለት፡- “ልጅህና ወንድምህ ለምኾን ለእኔ ቸርነትህ ይደረግልኝ፡፡ እነዚህን ሰዎች መልሰህ ወደ ጥበቃህ ትወስዳቸው ዘንድ ቅዱስነትህን እማፀናለሁ፡፡” እስከዚያ ግን መጠለያ ሰጥቷቸዋል፡፡ ዋና ተንከባካቢያቸው ማን ሊኾን እንደሚችል ማወቁ ቀላል ነው፤ ኦሎምፒያስ ነቻ!

ቴዎፍሎስ ግን ለቅዱስ ዮሐንስ ጥያቄ ሳይመልስ ዝም አለ፡፡ “እንዲያውም” ይላል ሶዞሜን “እንዲያውም በእስክንድርያ አከባቢ ቅዱስ ዮሐንስ እነዚህን መነኮሳት እንደ ተቀበላቸው፣ ከምሥጢራት እንዳካፈላቸው፣ ለእነርሱም ጥብቅና እንደ ቆመላቸው በማስመሰል ወሬ ተነዛ፡፡” ቅዱስ ዮሐንስ ግን ምንም ቢቀበላቸውም ከምሥጢራት አላካፈላቸውም፡፡ ክሳቸው ከከሰሳቸው ሰው መስማት ነበረበትና፡፡ ዳግመኛም በአንድ አገረ ስብከት የተከሰሰ ሰው በሌላ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሊፈታ አይችልምና፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም ኹለተኛ ደብዳቤ ላከለት፡፡ መነኮሳቱን ወደ እርሱ - ወደ ቴዎፍሎስ - እንዲመለሱ ቢጠይቃቸውም መመለስ እንደማይፈልጉ፣ እርሱ ራሱ (ቅዱስ ዮሐንስ) ነገሩን የማይፈታላቸው ከኾነም ወደ ንጉሡ ወደ አርቃድዮስ ሔደው ቴዎፍሎስን ሊከሱ እንዳሰቡና ነገሩ የተወሳሰበ እንዳይኾን መልካም ነው ብሎ በሚያስበው መንገድ ፈጥኖ መፍትሔ እንዲሰጠው የሚጠይቅ ደብዳቤ ነበር፡፡

ፓትሪያሪክ ቴዎፍሎስ በዚህ ጊዜ ደብዳቤ ጻፈ፤ ጠብን የሚያነሣሣ አሳብም ተናገረ፤ እንዲህ በማለት፡- “በጉባኤ ኒቅያ የተወሰነውና በአንድ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተያዘን ክስ በሌላ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሊፈታ እንደማይገባው የምታውቀው አይመስለኝም፡፡ ብታውቀው’ማ ኖሮ ተመልሰህ እኔን ባልወቀስከኝ ነበር፡፡ ደግሞም መከሰስ ካለብኝ በግብጻውያን ነገሥታት ፊት እንጂ ከዚህ የሰባ አምስት ቀን መንገድ ርቀህ በምትኖር በአንተ ፊት አይደለም፡፡” ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የቴዎፍሎስ የተንኰል ሥራ ምን እንደ ኾነ ስለማያውቅ የሚያስደነግጥ ኾነበት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ማድረግ ያለበትን ኹሉ ስላደረገ ከዚህ በላይ ምንም ላለማድረግ ወሰነ፡፡

መነኮሳቱምከዚህ በኋላ ወደ ንጉሡ ሔዱ፡፡ ሰኔ 402 ዓ.ም. በመጥምቁ ዮሐንስ ዓመታዊ በዓል ላይም ክሳቸውን አቀረቡ፡፡ በተለይም ነገራቸውን እንድታይላቸው የፈለጉት ንግሥት አውዶክሲያን ነበር፡፡ ንግሥቲቱም የሚቻላትን ኹሉ እንደምታደርግላቸው ቃል በመግባት ወደ አሌክሳንድርያ መልእክት ላከች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚመራው ጉባኤ ክሱ እንዲታይ ቴዎፍሎስን የሚጠራ ነበር፡፡ እንግዲህ ቅዱስ ዮሐንስ እንዳለው ነገሮች እንዴት እየተወሳሰቡ እንደሔዱ ተመልከቱ!

ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በቁስጥንጥንያ

ኤላጲዮስ የተባለ መልእክተኛ ከላይ የጠቀስነው መልእክት ይዞ ወደ ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ ተላከ፡፡ ፓትሪያሪኩም መልእክቱን ተቀበለ፡፡ የታዘዘውን ከማድረግ ውጪ አማራጭ አልበረውም፡፡ ነገር ግን ነገሮች እርሱ እንደሚፈልጋቸው ኾነው እንዲሔዱ አንድ ዘዴ ዘየደ፡፡ እርሱን ደግፈው የሚቆሙ ሰዎችን ማሰባበሰብ! በመኾኑም ወደ ቁስጥንጥንያ መሔድን ዘገየ፡፡ ዘግይቶ ተነሥቶም ቀጥታ ከመሔድ ይልቅ በፍልስጥኤምና በታናሽ እስያ ዞረ፡፡ ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ እንደ ተናገርን እርሱን ደግፈው የሚቆሙ ሰዎችን ለማሰባሰብ እንጂ፡፡ በዚህ ጉዞዉም የቅዱስ ዮሐንስ ቀንደኛ ጠላቶች የኾኑ አራት ሰዎችን አገኘ፡፡ ሦስቱ ጳጳሳት ሲኾኑ አንዱ መነኮሴ ነው፡፡ አካኪዮስ፣ አንቲዮኮስ፣ ሰቨሪያን እና ይስሐቅ ይባላሉ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በምግባረ ብልሹነታቸው ክህነታቸውን የያዘባቸው ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በልጅነቱ በአንጾኪያ እያለ ምን ዓይነት ጠባይ እንደ ነበረው እንዲመረምሩም አዘዛቸው፤ ቴዎፍሎስ፡፡

ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ ሌላም ሴራ ጎነጎነ፡፡ ይህን ሊያደርገው ያሰበውም በቅዱስ ኤጲፋንዮስ አማካኝነት ነበር፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ የኦሪገን ትምህርቶችን ይጠላ ስለ ነበርና ቴዎፍሎስም ይህን ስለሚያውቅ በዚህ ጎኑ ሊጠቀምበት አሰበ፡፡ በመኾኑም በቁስጥንጥንያ ኦርቶዶክሳዊ እምነት እየተፋለሰ እንደ ኾነና የዚህ መሪዉም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደ ኾነ በመግለጽ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ፈጥኖ ሊመጣ እንደሚገባ የሚገልጽ ደብዳቤ ጻፈለት፡፡

ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅንና የንጽህና እንጂ የነገር ሰው አልነበረምና ቴዎፍሎስን አመነው፡፡ መጋቢት 28 ቀን 403 ዓ.ም. በበዓለ ትንሣኤ ዕለትም ከቆጵሮስ ተነሥቶ ሚያዝያ አጋማሽ ላይ ቁስጥንጥንያ ደረሰ፡፡ መጀመሪያ የደረሰው ከላይ ስንጠቅሰው ወደ ነበረው ወደ መጥምቁ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ከእርሱ ጋር አብረው የመጡ ካህናት ነበሩና ቅዳሴ ሊቀድስ ፈለገ፡፡ አንድ ዲያቆንም ሾሞ ሥርዓተ ቅዳሴውን አከናወነ፡፡ ልብ በሉ! ይህን ኹሉ ሲያደርግ በአገረ ስብከቱ አይደለምና የቅዱስ ዮሐንስን ፍቃድ አልጠየቀም፡፡ በሌላ አገላለጽ ስናየው የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ሊቀ ጳጳስነት አልቀበልም እንደ ማለት ነበር፡፡

ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ወደ ቁስጥንጥንያ እንደሚመጣ ምንም መረጃ ያልነበረው ቅዱስ ዮሐንስ ከላይ የተናገርነውን እንደ ተከናወነ ሰማ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህ ለምን እንደ ተደረገ ስላላወቀ እንደ ጥንቱ ቅዱስ ኤጲፋንዮስን ጠራው፡፡ አገልግሎትና ጸሎት አብረው እንዲያከናውኑ፣ ማረፊያዉንም በመንበረ ጵጵስናው እንዲያደርግ ጠየቀው፡፡
ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ግን ዮሐንስ አፈወርቅ፡- ከግብጽ የመጡትን መነኮሳት አውግዞ ከቁስጥንጥንያ እስካላባረራቸውና የኦሪገንን መጻሕፍት እስካላወገዘ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚያድርበት ቤት ውስጥ አላድርም፤ አብሬውም አልቀድስም አለ፡፡ በዚህም ቅዱስ ዮሐንስ የኦሪገንን መጻሕፍት ካላወገዘ በራሱ ጊዜ ኦሪገናዊነቱን ያሳያል ብሎ አስቦ ነው፡፡ ተመልከቱ! ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ወደዚህ ኹሉ ውስብስብ ነገር የገባው በቴዎፍሎስ ነገረኛ ዘዴ ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጉባኤ ሊያደርግ እንዳሰበ፣ በዚያም እነዚያ ከግብጽ የመጡት መነኮሳት ኦሪገናውያን ስለ ኾኑ የተወገዙ እንደ ኾኑ፣ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም እነርሱን መልሶ ስላላባረራቸው ሊነቅፈው እንደ ተዘጋጀ ዐወቀ፡፡ ነገር ግን ነገሮችን በትዕግሥት ዐይቶ በሊቀ ዲያቆኑ አማካኝነት መልእክት ላከበት፤ እንዲህ ሲል፡- “ኤጲፋንዮስ ሆይ! ከቤተ ክርስቲያን ቀኖና ተቃራኒ የኾኑ ብዙ ነገሮችን አደረግህ፡፡ በመጀመሪያ በእኔ ሥር ባሉ አብያተ ክርስቲያናት እኔ ሳላውቅ ክህነት ሰጠህ፤ ገብተህ አገለገልህ፤ ጉባኤም አደረግህ፡፡ በዚህም ላይ ልቀበልህ ስል እምቢ አልህ፡፡ ወደ እኛ ትመጣ ዘንድ ብትጋበዝም አልተቀበልህም፡፡ ኹሉንም ነገር በራስህ ውሳኔ ታደርጋለህ፡፡ አሁንም ያደረግኸውና ልታደርገው ያስብከው ነገር ሊያመጣ ለሚችለው ሁከት ተጠያቂ እንዳትኾንና ራስህንም አደጋ ውስጥ እንዳትከት ተጠንቀቅ፡፡

ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ይህን ተግሣጽ እንደ ሰማ ወደ ቆጵሮስ ለመሔድ ጉዞ ጀመረ፡፡ ሶዞሜን እንደ ጻፈው መነኮሳቱ ቅዱስ ኤጲፋንዮስን አናግረዉት ነበር፡፡ ነገሩን ከእነርሱ ሲሰማም እየኾነ ያለውን ነገር ተረድቷል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅዱስ ዮሐንስን፡- “በመንበርህ እንዳለህ አትሞትም” እንዳለውና ቅዱስ ዮሐንስም፡- “አንተም ከመንበረ ጵጵስናህ አትደርስም” የሚል መልእክት እንደተለዋወጡ የሚገልጽ መረጃ አለ፡፡ ኹለቱም ያሉት ደርሷል፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ወደ መንበረ ጵጵስናው ሳይደርስ ግንቦት 12 ቀን 403 ዓ.ም. በባሕር ላይ ዐርፏልና፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ትንሽ ወረድ ብለን እናየዋለን፡፡

†††
ሊቁ በኦሪት ዘፍጥረት መጽሐፉ 11ኛው ድርሳኑ ላይ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ሲናገር፡- “ይህ ቅዱስ ሰው (ቅዱስ ጳውሎስ) ከደረሰበት ማዕርግ ጋር ፊት ለፊት ስገናኝ አንደበቴ እንደ ከባድ ጎርፍ ኾኖ መቈጣጠር አቃተኝ” እንዳለው እኔም ስለ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስናገር መቈጣጠር አቅቶኛልና ከዚህ በላይ ብቀጥል እናንተን ማድከም እንዳይኾን በቀጣይ ክፍል ብንጨርሰው ይሻላል!