Saturday, 31 October 2015

ተሀድሶ ክፍል ፰


           ብሉይ ኪዳን እንደ ዘመን፤                        

ዘመንን የሚያስነቅፈውም ሆነ የሚያስመሰግነው ሰው ነው። የሰው ልጅ፥በአዳም ኃጢአት ምክንያት፡- መርገመ ሥጋና መርገመ ነፍስ ወድቆበት ስለ ነበረ፥ ያን ዘመን የተነቀፈ እንዲሆን አድርጐታል። በሕገ ልቡና ዘመን እነ ኖኅ፥ ንጹሕ መሥዋዕት ቢያቀርቡም፥ በአዳም የውርስ ኃጢአት ምክንያት ዘመኑን ከመነቀፍ አላዳኑትም። የዘመናት ጌታ እግዚአብሔር ግን መሥዋዕቱን ውድዶ፣ ፈቅዶ በመቀበል፥ ቃል ኪዳን ሰጥቶአቸዋል። ዘፍ፡፰፥፳። እነ ሙሴም፡- በእግዚአብሔር በታዘዙት መሠረት፥ በሕገ ኦሪት እየተመሩ አምስት ዓይነት ንጹሐን መሥዋዕቶችን ሲያቀርቡ ኖረዋል። ዘጸ፡፲፪፥፭፣ ዘሌ፡ ከምዕራፍ ፩ እስከ ፭። ይህ ሁሉ የመሥዋዕት ዓይነት፥ ዘመኑን፡- ዘመነ ፍዳ፥ ዘመነ ኵነኔ ተብሎ ከመጠራት አልታደገውም። እነ ኢሳይያስን፡- “ጽድቃችንም እንደ መርገም ጨርቅ ነው፤” ያሰኛቸው፥ በክርስቶስ ቤዛነት ብቻ በተደመሰሰው የአዳም ኃጢአት ምክንያት እንጂ፥ ጽድቅ በራሱ የመርገም ጨርቅ ሆኖ አይደለም። ኢሳ፡፷፬፥፮። ስለዚህ የተነገረውን ቃል ጥሬውን መመገብ ሳይሆን፥የተተረጐመውን ብስሉን በማስተዋል መመገብ ይገባል። “እንዲህ ይላል፤”ማለት ብቻ ሳይሆን፥“ለምን እንዲህ ተባለ፤” የሚለውንም አብሮ ማየት ያስፈልጋል። ለምሳሌ፡- ሄሮድስ ሰው ሲሆን “ቀበሮ” ተብሎአል። ሉቃ፡፲፫፥፴፪። ፈሪሳውያን እና ሰዱቃውያን ደግሞ፥ “እፉኝት” ተብለዋል። ማቴ፡፫፥፯። 

                                                        

መሥዋዕት እንዲቀርብለት ያዘዘ እግዚአብሔር፥ ይመለከት የነበረው የቀረበውን መሥዋዕት ብቻ ሳይሆን፥ የአቅራቢውንም ሕይወት ነበር። “እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ፤” ይላል። ዘፍ፡፬፥፬። እግዚአብሔር የመሥዋዕት አቅራቢዎቹን በኃጢአት የቆሸሸ እና በበደል የረከሰ ሕይወት ሲነቅፍ ደግሞ፥ “በሬን የሚያርድልኝ ሰውን አንደሚገድል ነው፤ ጠቦትንም የሚሠዋ የውሻውን አንገት እንደ ሚሰብር ነው፤ የእህልን ቍርባን የሚያቀርብ የእርያን ደም እንደሚያቀርብ ነው፤ ዕጣንን የሚያጥን ጣዖትን እንደሚባርክ ነው። እነዚህ የገዛ መንገዳቸውን መረጡ፤ ነፍሳቸውም በርኵሰታቸው ደስ ይላታል፤ እኔ ደግሞ የተሳለቀባቸውን እመርጣለሁ፥ የፈሩትንም ነገር አመጣባቸዋለሁ፤ በፊቴ ክፉ ነገር አደረጉ፥ ያልወደድሁትንም መረጡ እንጂ በጠራሁ ጊዜ አልመለሱልኝምና፥ በተናገርሁም ጊዜ አልሰሙኝምና። ይላል። ኢሳ፡፷፮፥፫። ለሚሰሙትና ለሚታዘዙለት ግን እንዲህ አይደለም። ጻድቁ ካህን ዘካርያስ፡- የዕጣን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ባቀረበ ጊዜ፥ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጦለት፥ “ዘካርያስ ሆይ፥ ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ፥ ሚስትህም ኤልሳቤጥ ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፥ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ፤” ብሎታል። ሉቃ፡፩፥፰።                                                                              

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- በብሉይ ኪዳን ዘመን፥ የምሕረት ቃል ኪዳን ተሰጥቶአቸው ስለነበሩ ወገኖቹ ሲናገር፥ “ብዙ ኀዘን የማያቋርጥም ጭንቀት በልቤ አለብኝ ስል በክርስቶስ ሆኜ እውነትን እናገራለሁ፤ አልዋሽምም፤ ሕሊናዬም በመንፈስ ቅዱስ ይመሰክርልኛል። በሥጋ ዘመዶቼ ስለ ሆኑ ወንድሞቼ ከክርስቶስ ተለይቼ እኔ ራሴ የተረገምሁ እንድሆን እጸልይ ነበርና። እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና፤ አባቶችም ለእነርሱ ናቸውና፤ ከእነርሱም ክርስቶስ በሥጋ መጣ ፥እርሱም ከሁሉ በላይ ሆኖ ለዘላለም የተባረከ አምላክ ነው፤ አሜን።” ብሎአል። ሮሜ፡፱፥፩-፭። እንዲህም ማለቱ፡- ምሳሌውን ይዘው ከአማናዊው፥ ንባቡን ሰምተው ከትርጓሜው መድረስ ስለተሳናቸው ነው። የተነገረውን ትንቢት የተቈጠረውን ሱባዔ እያወቁ፥ በከንቱ በመቅረታቸው ነው ።እስራኤልን ችግር ላይ የጣላቸው፥ የኢየሱስ ክርስቶስ አመጣጥ፥ እነርሱ በጠበቁት መንገድና አኳዃን ባለመሆኑ ነው። በተለይም ፈሪሳውያን፡-“መሲሕ ሲመጣ የጦር ኃይል አቋቁሞ፥ ራሱ የጦር መሪ በመሆን፥ የሮማን የቅኝ ግዛት ቀንበር አውልቆ ጥሎ፥ የዳዊትን መንግሥት ያድሳል።” ብለው ይጠብቁ ነበር። ኤሴይ የሚባሉት ደግሞ፡- “መሲሕ ነጻ የሚያወጣን በተአምራት እንጂ በጦር ኃይ ል አይደለም፤” ይሉ ነበር። ሁለቱም ወገኖች፥ መሲሕ እንደሚመጣ፥ የተወሰኑ ምርጥ ጐሳዎችን ነጻ እንደሚያወጣ፥ ዓለም አቀፋዊ መሲሐዊ መንግሥት እንደሚይቋቁምና እነርሱም የመንግሥቱ ባለ ሟሎች እንደሚሆኑ ያምኑ ነበር። የዮሐንስና የያዕቆብ እናት ማርያም ባውፍልያ፥ ከልጆችዋ ጋር እየሰገደች፥ ሹመት የለመነችው ለዚህ ነው። “እነዚህ ሁለት ልጆቼ አንዱ በቀኝህ፥ አንዱም በግራህ ፥በመንግሥትህ እንዲቀመጡ እዘዝ።” ስትል መለመኗ፥ ቀኝ አዝማችነት እና ግራ አዝማችነት ሹምልኝ፥ ማለቷ ነበር።                                                                                 “ፊተኛው ኪዳን ነቀፋ ባይኖረው ለሁለተኛው ስፍራ ባልተገኘ ነበር፤”                                      

ይህ ኃይለ ቃል የሚያመለክተን፡-ሕገ ኦሪት እና መሥዋዕተ ኦሪት፥በሕገ ወንጌል እና በመሥዋዕተ አዲስ መተካታቸውን ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ከዚህ አያይዞ የተናገረው፥ የነቢዩ የኤርምያስ ትንቢት መፈጸሙን ነው። ምክንያቱም፡- ዕብራውያን የተነገረውን ትንቢት ጠንቅቀው ስለሚያውቁ ነው። “እነርሱን እየነቀፈ ይላቸዋልና፡- እነሆ ከእስራኤል ቤት(ከዐሥሩ ነገድ) ከይሁዳ ቤት(ከሁለቱ ነገድ) ጋር አዲስ ኪዳን የምገባበት ጊዜ ይመጣል ይላል ጌታ፤ ከግብፅ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደገባሁት ኪዳን አይደለም፤ እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው ይላል ጌታ።” የሚል ትንቢት ነበር። ኤር፡፴፩፥፴፩። እስራኤል፡-“ዘመኑን በዘመን ስለ አደሰው፥ አዲስ ሕግ እሠራላችኋለሁ አለ እንጂ፥ ሕጉስ ያው የጥንቱ ሕግ ነው።” እንዳይሉበት፥ አስረግጦ ነግሮአቸዋል። በዚህም፡- እንደ ኪዳነ ኖኅ፥እንደ ግዝረተ አብርሃም፥ እንደ ክህነተ ኦሪት፥ እንደ መሥዋዕተ ኦሪት ያለ አለመሆኑን አስቀድሞ ተናግሮአል። ምክንያቱም የመጀመሪያዋ  ሕግ ደግ ብትሆን ኖሮ ሌላ ደግ ሕግ ይሠራ ዘንድ ባልወደደም ነበር። የመጀመሪያ ው ለስርየተ ሥጋ ሲሆን፥ የሁለተኛው ለስርየተ ነፍስ ነው።        

የእስራኤል ልጆች ከግብፅ በወጡ በሦስተኛው ወር፥ ሙሴ፡- ወደ ደብረ ሲና ራስ፥ ወደ እግዚአብሔር ወጣ። እግዚአብሔርም ሙሴን፡- “በግብፃውያን ያደረግሁትን፥ በንስርም ክንፍ እንደ አወጣኋችሁ (ፈጥኜ ወደ እኔ ባለሟልነት እንደ አቀረብኳችሁ) አይታችኋል። አሁንም ቃሌን በእውነት ብትሰሙ፥ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፥ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት (ወገን) ትሆኑልኛላችሁ፤ እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ። (ቅዱሳን ነገሥታት፣ ቅዱሳን ካህናት እና ሃይማኖት የሚይዙ፥ ምግባር የሚሠሩ ምእመናን ከእናንተ ይወለዱልኛል።)” ብለህ ለእስራኤል ልጆች ንገር፥ ብሎት ነበር። ሙሴም የሕዝቡን አለቆች ጠርቶ  በነገራቸው ጊዜ፥ በአንድ ቃል፥ “እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ እናደርጋለን፤” ብለው ነበር። ዳሩ ግን እንደ ቃላቸው ሆነው ስላልተገኙ፥ “እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፤” ሲል ወቅሶአቸዋል፥ ቸልም እያለ በየጊዜው ለአሕዛብ አሳልፎ ይሰጣቸው ነበር። በዚህም፡- ከአምልኰተ እግዚአብሔር ወደ አምልኰተ ጣዖት ያፈገፈገ፥ ከገቢረ ጽድቅ ይልቅ ገቢረ ኃጢአትን ያዘወተረ ሰውነታቸው፥ በእግዚአብሔር ዘንድ የተነቀፈ ሆኖአል።                                                                                                                                           

        “ሕጌን በልቡናቸው አኖራለሁ፥በልባቸውም እጽፋለሁ፤”                   

እግዚአብሔር፡- በነቢዩ በኤርምያስ አንደበት የተናገረውን ቃል በመቀጠል፥ “ከዚያ ወራት በኋላ (አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም) ከእስራኤል ጋር የምገባው ቃል ይህ ነውና፤. . .ሕጌን በልቡናቸው እኖራለሁ፥ በልባቸውም እጽፋለሁ፥ እኔም አምላክ(አባት) እሆናቸዋለሁ፥ እነርሱም ሕዝብ (ልጆቼ) ይሆኑልኛል።” ብሎአል። በዚህም ልቡናቸውን ለቃለ እግዚአብሔር እንደሚከፍትላቸው ነግሮአቸዋል። በነቢዩ በኢሳይያስም፡- “ልጆችሽም ከእግዚአብሔር የተማሩ (እግዚአብሔር ልቡናቸውን ለቅዱስ ቃሉ የከፈተላቸው) ይሆናሉ።” ተብሎ ተነግሮአል። ኢሳ፡፶፬፥፲፫። ለምሳሌ፡- እግዚአብሔር የልድያን ልብ እንደ ከፈተላት በግብረ ሐዋርያት ተመዝግቦአል። የሐዋ፡፲፮፥፲፬። በአጠቃላይ አነጋገር፥ በመዓልትም በሌሊትም ሕጉን የሚያሰላስል ልብ እንደሚሰጠን የሚያመለክት ቃለ ትንቢት ነበር። በነቢዩ በሕዝቅኤል አንደበትም፡- “አዲስም ልብ እሰጣችኋለሁ፥ አዲስም መንፈስ በውስጣችሁ አኖራለሁ፤ የድንጋዩንም ልብ ከሥጋችሁ አወጣለሁ፥ የሥጋንም ልብ እሰጣችኋለሁ፤” ብሎአል። ሕዝ፡፴፮፥፳፮። ቅዱስ ዳዊት፡- “በዝንጉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ፥ የእግዚአብሔር ሕግ ብቻ ፈቃዱ የሆነ፥ ሕጉንም በቀንና በሌሊት የሚያስብ ምስጉን ነው።” ያለው ከላይ የተጠቀሰውን ዓይነት ልብ የተሰጠውን ሰው ነው። መዝ፡፩፥፩። በመሆኑም በርእሱ የተጻፈው ኃይለ ቃል መልእክት የተጻፈ ወንጌል፥ የተቀረጸ ጽላት አያስፈልግም ማለት እንዳልሆነ ማወቅም ማመንም ያስፈልጋል ። ለምሳሌ፡- እግዚአብሔር ከአዳም እሰከ ሙሴ ድረስ ሕዝቡን የመራው በሕገ ልቡና ነበር። መናፍቃኑ እንደሚሉት፥ የጽሑፍ ሕግ የማያስፈልግ ቢሆን ኖሮ፥ አገልጋዩን ሙሴን፡- ሕገ ኦሪትን አያጽፈውም ነበር፥ ጽላትም ቀርጾ አይሰጠውም ነበር። በአዲስ ኪዳንም፡- አርባዕቱ ወንጌላውያን፡- ቆዳ ፍቀው፥ ብራና ዳምጠው፥ ቀለም በጥብጠው፥ ብዕር ቀርጸው ወንጌልን ለመጻፍ አይደክሙም ነበር። ስለዚህ ልባችሁን ብራና (ወረቀት)፣ ጽላት አደርግላችኋለሁ ማለቱ፥ ለምን እንደሆነ በሃይማኖት ማስተዋል ይገባል። ለምሳሌ፡- ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡- ራሱን፥ “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤” በማለቱ፥ ደቀ መዛሙርቱንም፡- “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤” ስለ አላቸው፡- እርሱ የፈጠረው የፀሐይ ብርሃን፥ ሰው የሠራው የሻማ ብርሃን አያስፈልግም ማለቱ ይሆን? ማቴ፡፭፥፲፬፣ዮሐ፡፰፥፲፪።                                             

    “ወንድም ወንድሙን አያስተምርም፤”                                    

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው፡- “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፥ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ፤” ብሎ ነው። ማር፡፲፮፥፲፭። ራሱ ቅዱስ ጳውሎስም፡- “ወንጌልን ባልሰብክ ወዮልኝ፤” ብሎአል። ፩ኛ፡ቆሮ፡፱፥፲፮። ይህ እንዲህ ከሆነ፥ “ወንድም ወንድሙን አያስተምርም፤” ለምን ተባለ? ማለት ያስፈልጋል እንጂ፥ ጥሬ ንባቡን ብቻ ይዞ መከራከር ሰውን ከችግር ላይ ይጥላል። ስለዚህ፡- እግዚአብሔር ለትምህርተ ወንጌል፥ ልቡን ከፍቶለት ያመነውን ሰው፥ “እምነትህን በሥራ ግለጥ፤” ይባላል እንጂ፥ እንደ አዲስ አማኝ፥ “ጌታን ተቀበል፤” እንደማይባል ማስተዋል ተገቢ ነው። “እያንዳንዱም ጐረቤቱን፥ እያንዳንዱም ወንድሙን (በሃይማኖት የሚመስለውን ወንድሙን)፡- ጌታን እወቅ (እመን) ብሎ አያስተምርም፥ ከታናሹ ጀምሮ እስከ ታላቁ ድረስ ሁሉ ያውቁኛልና። ዓመፃቸውን እምራቸዋለሁና፥ ኃጢአታቸውንም ደግሜ አላስብም። ”ያለው ለዚህ ነው። ላልተማሩትን እና ላላመኑት ግን፡- “ጌታን እወቅ(እመን)፤” ብሎ ምሥጢረ ሥጋዌን ማስ ተማር ይገባል። “ጌታን እወቅ፥ብሎ አያስተምርም፤” የሚለውን ከነቢያት የጠቀሰ፥ ቅዱስ ጳውሎስ፡- “ለግሪክ ሰዎችና ላልተማሩም፥ ለጥበበኞችና ለማያስተውሉም ዕዳ አለብኝ፤ ስለዚህም በሚቻለኝ መጠን በሮሜ ላላችሁ ለእናንተ ደግሞ ወንጌልን ልሰብክ ተዘጋጅቼ አለሁ።”ብሎአል። ሮሜ፡፩፥፲፬።                     

  “አዲስ በማለቱ ፊተኛውን አስረጅቶአል፤”                   

     ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- የነቢዩን የኤርምያስን ትንቢት ከጠቀሰ በኋላ፥ ዕብራውያን ምዕራፍ ፰ን የደመደመው፡- “አዲስ በማለቱ ፊተኛውን አስረጅቶአል፤ አሮጌና ውራጅ የሆነውስ ሊጠፋ ቀርቦአል።” በማለት ነው። አነጋገሩ ምሳሌያዊ ነው፥ “ይህ ቤት ያማረ ያጌጠ ነበረ፥ ሊፈርስ ቀርቦአል፤ ይህ ልብስ የሞቀ የደመቀ ነበረ፥ ሊያልቅ ቀርቦአል፤” እንደ ማለት ነው።                    

በኦሪቱ፡-ከእንስሳት ወገን ንጹሕ የሆነ እና እንከን የሌለበት መሥዋዕት ተመርጦ ይቀርብ ነበር። ዘጸ፡፲፪፥፭፣ ዘሌ፡፳፪፥፳፬፣ ፩ኛ፡ጴጥ፡፩፥፲፰። አቅራቢው እጁን በእንስሳው ራስ ላይ በመጫን፥ ኃጢአቱን ያሸክመው ነበር። ዘሌ፡፩፥፬፤፲፮፥፳፩፣ ኢሳ፡፶፫፥፮፣ ፩ኛ፡ጴጥ፡፪፥፳፬። የኃጢአት ደመወዝ ሞት በመሆኑ፥ አቅራቢው፡- ኃጢአቱን የተሸከመለትን እንስሳ ያርደዋል። ሮሜ፡፮፥፳፫፣ ዕብ፡፱፥፳፭። ካህኑ ደግሞ፡- የመሥዋዕቱን ደም በእግዚአብሔር ፊት ያቀርባል። ዘሌ፡፩፥፭፤፲፯፥፲፩፣ ዕብ፡፱፥፲፪። እንደ መሥዋዕቱም ዓይነት፥ ከታረደው እንስሳ፥ልዩ ልዩ ክፍልና ብልት ያቃጥላል። ዘፍ፡፰፥፳፩፣ ሮሜ፡፲፪፥፩፣ ፪ኛ፡ ቆሮ፡፪፥፲፬፣ ኤፌ፡፭፥፪። “እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፡- አሮንን እና ልጆቹን እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፡- የሚቃጠለው የመሥዋዕቱ ሕግ ይህ ነው፤የሚቃጠለው መሥዋ ዕት በመሠዊያው ላይ ባለው እንጨት ላይ ሌሊቱን ሙሉ እስኪጸባ ድረስ ይሆናል፤ (የመሠዊያው እሳት እስኪነጋ ድረስ በበላዩ እየነደደ በመሠዊያው ላይ ይተዉት፥ ስቡንም በመሠዊያው ላይ ያቅልጡት)፤ እሳቱም በመሠዊያው ላይ ዘወትር ይነድዳል። (እሳቱ መሠዊያውን እንዳይጐዳው ደግሞ፥ ፈቀቅ አድርገው በጉድጓዱ ውስጥ ሲነድ ይደር)። ካህኑም የበፍታ (የነጭ ሐር) ቀሚስና የበፍታ ሱሪ በሥጋው ላይ ይለብሳል፤ በመሠዊያው ላይ የሚቃጠለውን መሥዋዕት እሳቱ ከበላው በኋላ አመዱን አንሥቶ በመሠዊያው አጠገብ ያፈስሰዋል። ልብሱንም (ነጩን የሐር ልብስ ያወልቃል፥ ሌላም(ተርታ) ልብስ ይለብሳል፤ አመዱንም ተሸክሞ ከሰፈሩ ንጹሕ ስፍራ ወደ ሆነ ወደ ውጭ ያወጣዋል። እሳቱም በመሠዊያው ላይ ዘወትር ይነድዳል፥ አይጠፋም፤ ካህኑም ማለዳ ማለዳ እንጨት ያቃጥልበታል፤ የሚቃጠለውንም መሥዋዕት በዚያ ላይ ይረበርባል፤ (በመሠዊያው ላይ እንጨት ይጨምር፥ በእንጨቱም ላይ ሊቃጠል የቀረበውን ሥጋ ያኑር)፥ በዚያም የደኅንነትን መሥዋዕት ስብ ያቃጥላል። (ድኅነት ሊደረግበት የተለየውንም ስብ ጨምሮ ያጢሰው)። ዘወትር በመሠዊያው ላይ እሳት ይነድዳል፥ አይጠፋም።” በማለት ነገረው፥ ይላል። ዘሌ፡፮፥፰-፲፫። ሐዋርያው፡- አሮጌና ውረጅ ያለው ይኸንን ነው።                                                                                             

በአዲስ ኪዳን ግን፥ ክርስቶስ እንጂ፥እንስሳት የሚሠዉባት ቤተክርስቲያን የለችንም ፥ ነፍስ የተለየው፥ እሳት መለኰት የተዋሀደው፥ የክርስቶስ ሥጋና ደም የሚፈተትባት እንጂ፥ የእንስሳት ሥጋ የሚቃጠልባት፥ ስቡም የሚጤስባት ቤተክርስቲያን የለችንም። መሥዋዕታችን፥ የአዲስ ኪዳን በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። “እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ፤” ይላል። ዮሐ፡ ፩፥፳፱፣፴፯። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም፡- “ፋሲካችን(የፋሲካ በግ) ክርስቶስ ታርዶአ ልና፤(እንደ ታረደ በግ፥ በመስቀል ላይ፥ሥጋውን ቆርሶልናልና፥ ደሙንም አፍስሶልናልና) ብሎአል። የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን።  
  

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን አገልግሎት እንድትጀምር ቅዱስ ሲኖዶስ ወሰነ፡፡

ሐራ ዘተዋሕዶ

የሳተላይት ሥርጭቱ መካከለኛው ምሥራቅን፣ ደቡብ አውሮፓንና ሰሜን አፍሪቃን ያካልላል

(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ ፲፮ ቁጥር ፰፻፳፬፤ ቅዳሜ፣ ጥቅምት ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም.)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሀገር ውስጥና በዓለም ዙሪያ ለሚገኙ አገልጋዮችዋ እና ምእመናንዋ ድምፅዋን የምታሰማበትና መረጃ የምትሰጥበት የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን አገልግሎት እንድትጀምር ቅዱስ ሲኖዶስ ወሰነ፡፡ ከጥቅምት 12 ጀምሮ የዓመቱን የመጀመሪያ የምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ በማካሔድ ላይ የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ፣የቴሌቪዥን አገልግሎቱን ለማስጀመር የሚያስችል የብር 12 ሚሊዮን 22 ሺሕ ዓመታዊ በጀት ከትላንት በስቲያ ማጽደቁ ታውቋል፡፡

በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የብዙኃን መገናኛ ድርጅት በሚል ተዋቅሮ ሥራ አስኪያጅ በመሠየምና እስከ 22 ሠራተኞችን በመቅጠር የሚጀምረው አገልግሎቱ፤ ዝግጅቱንና ቀረጻውን በሀገር ውስጥ በማከናወንበሳተላይት እንደሚሠራጭ ተገልጧል፡፡

በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያ ተልእኮ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራውና ዘጠኝ አባላት ያሉት የብዙኃን መገናኛ ቦርድ፤ የሳተላይት ሥርጭት አገልግሎት የሚሰጠውን የኮሚዩኒኬሽን ኩባንያ በመምረጥ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡

ባለፈው ማክሰኞ በሚዲያ ጥቅም፣ አሠራርና የወደፊት አቅጣጫ ዙሪያ ለምልአተ ጉባኤው አባላት ማብራሪያ የሰጡት የቦርዱ አመራሮች፤ የሳተላይት ሥርጭቱ ለጊዜው መካከለኛው ምሥራቅን፣ ደቡብ አውሮፓን፣ ሰሜንና ምሥራቅ አፍሪቃን የሚያካልል እንደኾነና ለተቀረው ዓለም ዝግጅቱን በኢንተርኔት በመጫን እንደሚያስተላልፍ አስረድተዋል፡፡

መምሪያው፣ የብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎችን በማስተባበር ያስጠናውን የአገልግሎቱን መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ ባለፈው ዓመት ግንቦት በቅዱስ ሲኖዶሱ አጸድቋል፤ በቀጣይም የሬዲዮ ሥርጭት ለመጀመር መታቀዱ ተጠቁሟል፡፡ ሥራውን ለማስጀመር የሚያስችል መሠረታዊ የኦዲዮ ስቱዲዮ በመንበረ ፓትርያርኩ የሚገኝ ሲኾን አገልግሎቱ የሚፈጥረው የፋይናንስ አቅም ወሳኝነት ይኖረዋል፡፡

የቴሌቭዥን አገልግሎቱን የ24 ሰዓት ሥርጭት ለማስጀመር ያኽል የጸደቀው የአንድ ዓመት በጀት በጠቅላይ ጽ/ቤቱ የሚሸፈን ሲኾን ለዘለቄታው ከማስታወቂያ፣ ከአየር ሰዓት ሽያጭና ከበጎ አድራጊዎች በሚገኘው ድጋፍ አገልግሎቱን ያጠናክራል፤ ተብሏል፡፡ በአሌክሳንደርያ ተዘጋጅቶ ቆጵሮስ እና ሰሜን አሜሪካ በሚገኙ የሳተላይት ኩባንያዎች የሚሠራጨው የግብጹ ኮፕቲክ ቴሌቭዥንወጪ የቤተ ክርስቲያኒቱ ምእመን በኾኑ ባዕለጸጋ መሸፈኑም አገልግሎቱን በፋይናንስ ከመደገፍ አኳያ ለኢትዮጵያውያን ኦርቶዶክሳውያን ባለሀብቶች የሚያስገነዝበው ትልቅ ቁም ነገር አለው፡፡

በሀገር ውስጥና በዓለም ዙሪያ ከ50 ሚሊዮን በላይ አገልጋዮችና ምእመናን ያሏት ቤተ ክርስቲያን፤ከሬዲዮና ከቴሌቭዥን ነባር ሚዲያዎች በተጨማሪ ዘመኑ የሚጠይቀውን የመገናኛ ቴክኖሎጂ ተጠቅማ ምእመናንዋን መጠበቅና ማስተማር ካልቻለች በተለይም ተተኪውን ወጣት ትውልድ ለመድረስ እንደሚያስቸግራት፣ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ይናገራሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ የብዙኃን መገናኛ ሥርጭት ጥናቱ ሲጀመር ከተመደቡት ሦስት ብፁዓን አባቶች ጋርየሚዲያ ጥናት እና የገቢ አሰባሳቢ ኮሚቴውን በማስተባበር፤ በግብጽና በእስራኤል ያሉ ተሞክሮዎችን በመዳሰስ፤ የሚዲያ ባለሞያዎችን በማትጋት ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡

ብፁዕነታቸው፣ “ሚዲያ እና ዓለምአቀፋዊ አስተሳሰብ”በሚል ርእስ ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ የ24 ሰዓት የሳተላይት ሥርጭት የሚጀምረው የቴሌቪዥን አገልግሎቱ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነቷን፣ ሥርዐተ እምነቷን፣ ክርስቲያናዊ ትውፊቷንና ታሪኳን ለማስተማር፤ ቅዱሳት መካናቷንና ቅርሶቿን ለማስተዋወቅ፤ ተማሪዎችንና ምሁራኑን ለጥናትና ምርምር ለማነሣሣት፤ በየአህጉረ ስብከቱ የተሠሩ መልካም ሥራዎችን በማስፋፋትና ተቀራርቦ በመሥራት የምእመኑን ጠንካራ ድጋፍ ለማግኘት የግድ ያስፈልጋታል፤ ብለዋል፡፡

Friday, 30 October 2015

በጥንት ዘመን ተፈልጎና ጳጳስ ኹን ተብሎ ተለምኖ ነበረ፤ አኹን ግን ሹሙኝ እያሉ የሚመጡ ሰዎች ናቸው ያሉት /አቡነ ማትያስ /

በዕጩዎቹ ምርጫ የገዳማት ጥቆማ ቅድሚያ ትኩረት ይሰጠዋል
ምርጫውንና ውድድሩን ከሲሞናዊነት ለመጠበቅ ይረዳል፤ ተብሏል
የካህናቱ እና የሕዝቡ ምርጫ እና ምስክርነትስ?

የዕጩ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ እና ሹመት፣ በመጪው ግንቦት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንደሚፈጸም ተጠቆመ፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ በትላንት ስምንተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው፣ የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ጥናት በሚል በያዘው አጀንዳ÷ ዕጩዎቹ፣ ምልአተ ጉባኤው በወቅቱ በሚሠይመው አስመራጭ ኮሚቴ ተገምግመውና ተመዝነው ለውድድር እንዲቀርቡ ወስኗል፡፡

በዕጩዎቹ ምርጫ፣ በገዳማት ለሚጠቆሙ መነኰሳት እና ቆሞሳት የቅድሚያ ትኩረት እንደሚሰጠው ተገልጧል፡፡ ይህም የዕጩዎችን ሥርዐተ ምንኵስና ለመፈተሽ እና ለኤጲስ ቆጶስነት በሚያበቃው መስፈርት መሠረት ተቀባይነት ያለው ምርጫ በማካሔድ ምርጫውንና ሹመቱን ከሲሞናዊነት ለመጠበቅ እንደሚረዳ ታምኖበታል፡፡

በሞተ ዕረፍት የተለዩትና በዕርግና የሚገኙት ብፁዓን አባቶች ቁጥር፣ በበርካታ አህጉረ ስብከት እና ተቋማት ከፈጠረው የአስተዳደር ክፍተት አንጻር የኤጶስ ቆጶሳት ሹመት አስፈላጊነት በቅዱስ ሲኖዶሱ ቢታመንበትም፣በስደት ካሉት አባቶች ጋር በተጀመረው ዕርቀ ሰላምና የምርጫ ሥርዐቱን ከማሻሻል ጋር ተያይዞ ሳይፈጸም ቆይቷል፡፡

ምርጫው በአኹኑ ምልዓተ ጉባኤ ተከናውኖ ሹመቱ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በዓለ ሢመት እንዲፈጸም ሐሳብ ቀርቦ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡ ይኹንና “ማንን ነው የምንሾመው? በዚኽ ጊዜ እንዴት ነው የምንሾመው” የሚለው የርእሰ መንበሩ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ጥያቄ፣ ሒደቱ ለሹመት ባሰፈሰፉና ከሹመቱ ለመጠቀም በቋመጡ ሲሞናውያን ፈተና ውስጥ መግባቱን ያረጋገጠ ኾኗል፡፡

የጥቅምት እና የግንቦት ምልዓተ ጉባኤ ስብሰባዎች በተቃረቡ ቁጥር ሹመቱን ለኖላዊነት እና ለአገልግሎት ሳይኾን ለድሎት እና ለፍትፍት የሚሹ ተስፈኞች ደጅ ጥናት እና ግርግር በገሃድ ይታያል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩም፣ “በጥንት ዘመን ተፈልጎ፣ ና ጳጳስ ኹን ተብሎ ተለምኖ ነበረ፤ አኹን ግን ሹሙኝ እያሉ የሚመጡ ሰዎች ናቸው ያሉት፤” ሲሉ ነው ኹኔታውን የገለጹት፡፡

እንደ ፍትሐ ነገሥቱ ሥርዐተ ሢመተ ክህነት፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ እና ውሳኔ በአንብሮተ እድ በሚሾመው ኤጲስ ቆጶስ ምርጫ፣ የካህናት እና የሕዝቡ ምስክርነት የራሱ ሚና አለው፡፡ ኤጲስ ቆጶስ ሲሾም ካህናቱም ሕዝቡም በሙሉ ተገኝተው እየመሰከሩለት ነው የሚሾመው = “ወኵሉ ሰብአ ይኅበሩ በእንተ ተሠይሞቱ ሕዝበ ወካህናት እንዘ ስምዐ ይከውን ሎቱ”/ፍት. መን. አንቀጽ ፭/

ካህናት እና ሕዝቡ እንዲሾምላቸው ኤጲስ ቆጶስ የሚኾነውን ቆሞስ መርጠው ሲያቀርቡ ስለ ደግነቱና ትሩፋቱ፤ ስለንጽሕናውና ከነውር የራቀ ስለመኾኑ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ሦስት ጊዜ እየመላለሰ ማረጋገጫ ይጠይቃቸዋል፡፡ ሕዝቡም አረጋግጠው “የሚባለው ነው” ብለው ሦስት ጊዜ መልስ ይሰጣሉ፡፡ በሦስተኛው ሕዝቡ መልስ ሲሰጡ እጃቸውን አንሥተው“ይገባዋል” እያሉ ያጨበጭባሉ ወይም አመልጥነው“አማን በአማን” እያሉ ያሸበሽባሉ፡፡ ካጨበጨቡ በኋላ ተቃውሞ ቢነሣ ያስታርቃሉ እንጂ ተቀባይነት የለውም፡፡ /ፍት. ነገ. አንቀጽ ፭ ረስጠብ ፶፪/

Thursday, 29 October 2015

የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄን ለመከላከል እና ለማጋለጥ በመካሔድ ላይ የሚገኘው እንቅስቃሴ በቋሚ ኮሚቴ እንዲመራ ወሰነ፡፡

የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄን በትምህርት ይከላከላል፤ ማስረጃዎችን እያቀረበ ያጋልጣልየጠቅ/ቤተ ክህነቱ የፀረ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ቋሚ ኮሚቴ በብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ይመራልቋሚ ኮሚቴው፣ ከሰርጎ ገቦች የጸዳና አባላቱም በሃይማኖታቸው እንከን የሌላቸው ሊኾኑ ይገባል

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፤የካፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊ እና ታሪካዊ ትውፊት እንዳይፋለስ መጠበቅ እና ማስጠበቅ፤ አገልግሎቷ እና አስተዳደሯ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንዲመራ የማድረግ ሓላፊነት ያለበት ቅዱስ ሲኖዶስ÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄን ለመከላከል እና ለማጋለጥ በመካሔድ ላይ የሚገኘው እንቅስቃሴ በቋሚ ኮሚቴ እንዲመራ ወሰነ፡፡

ቋሚ ኮሚቴው÷ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዐተ እምነት እና ክርስቲያናዊ ትውፊት በመበረዝ እና አስተዳደራዊ አንድነቷን በማናጋት ለመከፋፈል አልያም ባለችበት አዳክሞ ለመውረስ ወደ መዋቅሯ ሰርገው የገቡትን የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችንና የዋነኛ አዝማቾቻቸውን ሤራ በማስረጃ የማጋለጥ እና በትምህርት የመከላከል ተልእኮ የተሰጠው ሲኾን ተግባሩን የሚያስፈጽምበት መዋቅርም በዘላቂነት እንዲዘረጋ ነው የተወሰነው፡፡

ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አህጉረ ስብከት እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ የሚዘረጋው የፀረ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ቋሚ ኮሚቴ በበላይነት የሚመራው በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ሲኾን በቋሚ ኮሚቴው አባልነት የሚመረጡት ሊቃውንት፣ ካህናት፣ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችም በእምነታቸው እንከን የሌለባቸው፤ በቀናዒነታቸው፣ በዕውቀታቸው እና በሕይወታቸው የተመሰከረላቸው ሊኾኑ እንደሚገባ ቅዱስ ሲኖዶሱ በውሳኔው ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

‹‹መምህር›› ግርማ የተጠረጠሩበት ወንጀል ዝርዝር ይፋ ሆነ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 18 ፣ 2008 ( ኤፍ .ቢ .ሲ )

ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት መምህር ግርማ ወንድሙ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበዋል። መምህር ግርማ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄም ወድቅ ተደርጓል።

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፖሊስ መርማሪ ቡድን ዛሬ ግለሰቡን በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት አቅርቧቸዋል። ፖሊስ ግለሰቡ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ቀሪ የምርመራ ስራ ስላሉብኝ ተጨማሪ 14 ቀን ይፈቀድልኝ ብሏል።

ተጠርጣሪው በራሳቸውና በጠበቃቸው በኩል ፖሊስ የጠየቀውን ተጨማሪ ጊዜ በመቃወም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል። የፖሊስ የምርመራ ቡድን በበኩሉ እሳቸው ቢለቀቁ ሌሎች ተፈላጊዎችን እና የተለያዩ ሰነዶችን ስለሚያሸሹብን ጥያቄያቸው ውድቅ ይሁን ብሏል። ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ አብዛኛውን የምርመራ ስራ ያካሄደ በመሆኑ ለቀሪ የምርመራ ስራዎቹ ይረዳል በማለት ከጠየቀው የ 14 ቀን ጊዜ ውስጥ 7 ቀን ብቻ ፈቅዷል። ውጤቱን ለመጠባበቅም ለጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።

የወንጀሉ ዝርዝር

ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ. ም ነው ብሏል። በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው። እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።

እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል። የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ 800 ሺህ ብር ይሸጡታል። ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው
የሚለው የምርመራ መዝገቡ።

ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው። ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።

የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን. ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው። ተጠርጣሪው እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።

ጠበቃቸውም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል አይደለም፤ ፖሊስም የሚጠበቁ ምርመራዎቹን አጠናቋል፤ ደንበኛዬ የዋስትና መብታቸው ይከበርልኝ በማለት ጠይውቋል። ይሁን እንጂ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጓል።

Wednesday, 28 October 2015

የአዲስ አበባ ፖሊስ፣ አጥማቂ ነኝ ባዩን ግርማ ወንድሙን በቁጥጥር ሥር አዋለ።

(ኤፍ ቢ ሲ፤ አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም.)

የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ምንጮች፣ መምህር ግርማ ዛሬ በፖሊስ በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው መኾኑን ተናግረዋል።

አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ፣ በማጥመቅ እፈውሳለኹበሚል በተለያዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሕገ ወጥ ሀብት ሲያካብት እና በርካታ ምእመናንን ለችግር ሲዳግር ቆይቷል፡፡

ይኹን እንጂ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ያነገጋረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ አጥማቂው ዕውቅና እና ፈቃድ የተነፈገው ሕገ  ወጥ  እንደኾነ  አረጋግጧል።

የፋና ምንጮች፣ አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ በፈውስ አገልግሎት ስም የማጭበርበር ወንጀል ሳይጠረጠር እንዳልቀረ ነው የተናገሩት።

ሰበር ዜና – ፈቃድ የሌላቸው የኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራሞች በቤተ ክርስቲያን ስም እንዳይጠቀሙ ተወሰነ፤ ቤተ ክርስቲያኗ የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት ትጀምራለች


ሐራ ዘተዋሕዶ እንደዘገበው 

የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ እና ዕውቅና የሌላቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ ቃለ ዐዋዲ” በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል

በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ መሠረት፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የብዙኃን መገናኛ ቦርድ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው

በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ላይ የቀረቡ ማስረጃዎች የበለጠ ተጠናክረው አጀንዳው በልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ተወስኗል

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ከማእከል የተሰጠ ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው  በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም፣
በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ (EBS) የቴሌቭዥን ጣቢያ፣ “ሃይማኖታዊ ትምህርት” የሚያስተላልፉ ፕሮግራሞች፣ የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ ወሰነ፡፡

ምልአተ ጉባኤው በዛሬ፣ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ስድስተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው ያሳለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲኾን፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቭዥን በደብዳቤ እንዲያውቁት ይደረግ ዘንድ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡

በውሳኔው÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በስም የተጠቀሱ ሲኾን በፕሮግራሞቹ አዘጋጅነት የሚታወቁት በተለይ የ“ታዖሎጎስ” ግንባር ቀደም ምንደኞች፣ ፕሮግራማቸው “ራሱን የቻለ የሚዲያ ተቋም” እንጂ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ይኹን ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በይፋ በሰጡት መግለጫ ማረጋገጣቸው ይታወሳል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ከዚሁ ጋር በማያያዝ፤ በሊቃውንት ጉባኤ ሳይመረመሩ እና በማእከል ሳይፈቀዱ በግለሰቦች እየተዘጋጁ የቤተ ክርስቲያንን ስም ይዘው ስለሚወጡ የስብከት፣ የመዝሙር እና የመጻሕፍት ኅትመቶች እንዲኹም የአዳራሽ ጉባኤያት እና ስብሰባዎች ከተወያየ በኋላ ቀደም ሲል ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች በማጽናት ተመሳሳይ ትእዛዝ መስጠቱ ታውቋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ስብከተ ወንጌል እና ሚዲያን በተመለከተ” በተራ ቁጥር ሦስት በያዘው አጀንዳ፤ ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊነቱን ጠብቆ የራስዋን ድምፅ ለዓለም የምታሰማበት እና ስብከተ ወንጌልን የምታስፋፋበት የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት እንዲጀመርም ወስኗል፡፡

ለቤተ ክርስቲያን የብዙኃን መገናኛ ስርጭት የሚያስፈልገውና በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አስተባባሪነት ተጠንቶ የቀረበው በጀት ባለፈው ዓመት ግንቦት በምልአተ ጉባኤው የጸደቀ ሲኾን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር እንደተመለከተው፤ በዚኽ ዓመት በጀቱ በአፋጣኝ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበውን ጥያቄ በመቀበል የፋይናንስ ምንጮቹን ወስኖ ለነገ የሚያቀርብ ሦስት አባላት ያሉት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት(ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ) ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤ ተሠይሟል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ባለፈው ዓመት ግንቦት ባጸደቀው የሚዲያዎች (የሬዲዮ እና የቴሌቭዥን አገልግሎት) ሥርጭት ደንብ መሠረት፤ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራ የብዙኃን መገናኛ የሥራ አመራር ቦርድ የተቋቋመ ሲኾን ተግባሩን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ለ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ የቀረበው ሪፖርት ያስረዳል፡፡

በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ስብከተ ወንጌልን ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በአጽናፈ ዓለም ለማስፋፋት እና ለማጠናከር ስለሚያስፈልጓት ሚዲያዎች፣ በመምሪያው አስተባባሪነት በብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎች የተካሔደውን ጥናት መሠረት አድርጎ መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ/ማኑዋል ተዘጋጅቷል፡፡

በተያያዘ ዜና፣ “የቤተ ክርስቲያኗን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ማየት” በሚል ዐቢይ አጀንዳ ሥር በፊደል ተራ ቁጥር 4/መ፣ “የተሐድሶ እንቅስቃሴን በተመለከተ” ፤ የተዘጋጀው ሰነድ በተጨማሪ ማስረጃዎች ተስፋፍቶ እና ተጠናክሮ ራሱን በቻለ ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል፡፡

የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፤ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ግንባር ቀደም መሪዎች በሚሰጣቸው ተልእኮ እና ድጋፍ በቤተ ክርስቲያናችን የአስተዳደር እና የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በመስረግ የኑፋቄውን አስተሳሰብ እና ድርጊት የሚያራምዱ የ66 አካላት እና ግለሰቦች የሰነድ፣ የምስል እና የድምፅ ማስረጃዎች ከኃምሳ ገጾች ማብራሪያ ጋር ተደግፎ ተዘጋጅቷል፡፡

ቸር ወሬ ያሰማን